- በአገራችን በሰው የመነገድና ሰውን በሕገ-ወጥ መንገድ ድንበር የማሻገር ወንጀሎችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በአጠቃላይ የፍልሰት አስተዳደሩን በተቀናጀ ሁኔታ ለማስተዳደር በአዋጅ ቁጥር 1178/12 መሠረት በክቡር ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመራ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጠሪ የሆነ የፌደራል ተቋማት መሪዎች፣ የክልል ርዕሳነ መስተዳድሮችና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማትን ያካተተ ብሔራዊ ም/ቤት ተቋቁሟል፤
- በፌደራል ደረጃ ለም/ቤቱ ተጠሪ የሆነ በሚኒስቴር መስሪያ ቤታችን የሚመራ የተለያዩ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማትን ያካተተ ብሔራዊ የፍልሰት ትብብር ጥምረት ተቋቁሟል፡፡
- ተቋማችንም የፌደራል መንግስቱ የሕግ አማካሪ፣ የሰብዓዊ መብት የድርጊት መርሃ ግብር አፈጻጸምን የሚያስተባበር፣ የወንጀል መከላከል ፖሊሲና ስትራቴጂውን አተገባበር የሚያስተባብር፣ የፌደራል ሕጎችን ተፈጻሚነት የሚከታተል፤ ለበሕግ ጉዳዮች ዓለም አቀፍ ትብብር ሴንትራል ኦቶሪቲ የሆነ እንዱሁም የተመድ የተደራጁ ወንጀሎች ፕሮቶኮልና ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመከላከል የወጡትን ፕሮቶኮሎች አፈጸጸም በበላይነት እንዲያስተባብር በአዋጅ ሥልጣን የተሰጠውና ሌሎችም ትላልቅ አገራዊ አንድምታዎች ያላቸው ኃላፊነቶች የተጣሉበት በመሆኑ በፖሊሲ ውሳኔ የትብብር ጥምረቱን የመምራት ኃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡
- በተቋማችን የሚመራው ብሔራዊ የትብብር ጥምረት ወንጀሎቹን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠር እና ተጎጂዎችን መልሶ ለማቋቋም እንዲሁም መደበኛ ፍልሰትን ለማበረታታት የሚያስችሉ ጥናቶችን በማጥናት፣ ፖሊሲዎችን፣ ስትራቴጂዎችን፣ ህጎችን የማዘጋጀት፣ ለብሔራዊ ምክር ቤቱ የማቅረብ እና አግባብ ባለው አካል ሲጸድቅም ተግባራዊነቱን የማስተባበር፤ ተጎጂዎችን ማዳን፣ መልሶ ማቋቋምና ልዩ ልዩ ድጋፍ ስለሚገኙበት ሁኔታ አገር አቀፍ የቅብብሎሽ ስርዓት መመሪያ የማዘጋጀትና ሲጸድቅም አተገባበሩን የመከታተል፤ ስለ አገር ውስጥ መፈናቀል፣ ስደትና ፍልሰት፣ የስራ እድል ፈጠራና መሰል ጉዳዮች የፖሊሲ፣ የሕግና ስትራቴጂ ማዕቀፍና የአሠራር ስርዓት እንዲዘጋጅ ማስተባበርና ሲጸድቅም አተገባበሩን የመከታተል እና ሌሎች ኃላፊነቶች ተሰጥተውታል፡፡
- ጥምረቱ በአዋጁ የተጣሉበትን ተግባርና ኃላፊነቶች በአግባቡ እንዲወጣ ለማስቻል የፍልሰት ዋና ዋና የትኩረት መስኮችን መሠረት በማድረግ በስድስት የሥራ ቡድኖች እንዲደራጅ የተደረገ ሲሆን፤ እነዚህም
- የግንዛቤ ፈጠራ የስራ ቡድን- በኢፌዴሪ የሴ/ማ/ዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የሚመራ፤
- የሕግ ማስከበር የሥራ ቡድን- በተቋማችን የጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ዘርፍ የሚመራ፤
- የተጎጂዎች ድጋፍ፣ መልሶ ማቋቋምና የውጭ አገር ሥራ ሥምሪት የስራ ቡድን- በኢፌዴሪ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የሚመራ፤
- የዳያስፖራ ተሳትፎና ልማት የስራ ቡድን- በኢ/ያ የዳያስፖራ አገልግሎት የሚመራ፤
- የፍልሰት መረጃና አስተዳደር የስራ ቡድን- በኢ/ያ ስታትስቲክስ አገ/ት የሚመራ፤
- የፍልሰት ምርምር የስራ ቡድን- በኢፌዴሪ የትምህርት ሚኒስቴር የሚመራ ናቸው፡፡
- በዚሁ መነሻ ሴክሬታሪያቱ የተሰጠው ኃላፊነት ተቋማችን እንደመሪ የተጣለበትን ጥምረቱን፣ የስራ ቡድኖችንና አባል ተቋማትን የመደገፍና የማስተባበር ኃላፊነቱን መወጣት እንዲሁም እንደአንድ አባል ተቋም የተሰጠውን ሚና (በሌሎች የስራ ክፍሎች ከሚከናወኑት ኦፐሬሽናል ስራዎች በቀር) መወጣት ነው፡፡