በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የጥብቅና ፈቃድ አስተዳደርና ነፃ የሕግ ድጋፍ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ከተገልጋዮች የሚቀርብ የጥብቅና ፈቃድ ይሰጠኝ ጥያቄን በመቀበል መስፈርቱን አሟልተው ለተገኙ 254 የጥብቅና ፈቃድ የሰጠ መሆኑን የዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ፍቃዱ ደምሴ ገለጹ፡፡
በሕጉ ላይ የተቀመጠውን የጥብቅና ፈቃድ አሰጣጥ መስፈርት አሟልተው ፈቃድ ለመውሰድ ለሚፈልጉ 377 አዲስ የጥብቅና ፈቃድ ከጠየቁት ሰዎች መካከል አግባብነት ያላቸው ማስረጃዎችን ላቀረቡ 254 ፈቃድ ጠያቂዎች የጥብቅና ፈቃድ ሲሰጣቸው ቀሪዎቹ 123 የጥብቅና ፈቃድ እንዲወስዱ ተፈቅዶ ፈቃዱን ያልወሰዱና መልቀቂያቸውን ባለማቅረባቸው እና ሌሎች ማስረጃዎች ባለሟሟላታቸው የጥብቅና ፈቃድ ለጊዜው እንዳያገኙ የተደረጉ መሆኑን አቶ ፍቃዱ ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል ጠበቆች የጥብቅና ፍቃዳቸውን ለማደስ ሲመጡ በማህደራቸው ውስጥ ግብር የተከፈለበት ደረሰኝ መኖሩን፣ ክሊራንስ ማቅረባቸውን የሚያሳይ ማስረጃ ማቅረባቸውን፣ ከቅጣት ነጻ መሆናቸውን እና ነጻ የጥብቅና አገልግሎት ስለመስጠታቸው የሚገልጽ ማስረጃ መኖሩን የሚገልጹ መስፈርቶች ከታዩ በኋላ ለ1885 የፌዴራል ፍ/ቤቶች ጠበቆች የእድሳት አገልግሎት መሰጠቱን አቶ ፍቃድ አክለው ገልጸዋል፡፡
አያይዘውም ከነዚህም ውስጥ 1713 የፌዴራል ማናቸውም ፍ/ቤት ጠበቆች ሲሆኑ 172 ደግሞ የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት ጠበቆች መሆናቸውን አውስተዋል፡፡
የጥብቅና ፈቃድ አስተዳደርና ነጻ የሕግ ድጋፍ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ከላይ ከተጠቀሱት ተግባራት ባሻገር የጥብቅና ፈቃድ በአደራ ይቀመጥልኝ በሚል የሚቀረቡ ጥያቄዎችንም ተቀብሎ እንደሚያስተናግድ የጠቆሙት ዳይሬክተሩ በበጀት ዓመቱ ግማሽ ዓመት 31 የሚሆኑ ፈቃዱ በአደራ ይቀመጥልኝ በሚል ጥያቄ ያቀረቡ ጠበቆች ፍቃዳቸው በአደራ እንዲቀመጥላቸው መደረጉን አክለው ገልጸዋል፡፡