የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የሴቶች፤ ሕፃናት እና ባለ ብዙዘርፍ ጉዳዮች ዳሬክቶሬት ከUN-Women እና የአፍሪካ አመራርነት ልህቀት አካዳሚ (AFLEX) ጋር በመተባበር “የለውጥ አመራርነት ለሥርዓተ-ጾታ እኩልነት” በሚል ርዕሰ ላይ ያተኮረ ሥልጠና ለተቋሙ እንዲሁም ለተጠሪ ተቋማት ሴት አመራሮች ሰጠ፡፡
በተባበሩት መንግስታት የUN-Women የኢትዮጵያ ተወካይ ሚስተር ሻድራክ በመድረኩ እንደተናገሩት በቂ የሆነ ክህሎት ያላቸው ሴት አመራሮችን ማፍራት የሥርዓተ-ጾታ እኩልነት እንዲረጋገጥ ለማድረግ የማይተካ ሚና እንዳለው ጠቅሰው፤ በተለይ በፍትሕ ዘርፉ ውስጥ የለውጥ አመራርነት ክህሎት ያላቸው ሴቶች መኖራቸው በህገ-መንግስቱ እና በተለያዩ ኮንቬንሽኖች ለሴቶች የተሰጡ መብቶችን ለማስጠበቅ እንዲሁም የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥ አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው አስረድተዋል፡፡
በፍትሕ ሚኒስቴር የተቋም ግንባታና ሪፎርም ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር ዶ/ር ኤርምያስ የማነብርሃን በበኩላቸው የሴቶችን የአመራርነት ክህሎት ከማሳደግ አኳያ የለውጥ አመራርነት ክህሎት ትልቁን ሚና እንደሚጫወት ገልፀው፤ ፍትሕ ሚኒስቴር ሴቶችን ከማብቃት እና ለጉዳዩ ትኩረት ከመስጠት አንፃር ሊተገበር የሚገባ ስለሆነ መስል ጉዳዮች ላይም በቀጣይ ተቋሙ በስፋት የሚሰራበት ይሆናል ብለዋል፡፡
በፍትሕ ሚኒስቴር የሴቶች ሕፃናት እና ባለዘርፍ ጉዳዮች ዳሬክቶሬት ወ/ሮ ዳግማዊት አላምኔ ሥልጠናው በተለይ የአመራርነት መሰረታውያን፤ ኮሙኒኬሽን እና ግጭትን ማስተዳደር፤ራስን ማብቃት፤ ሥርዓተ-ጾታ እና አመራርነት በሚሉ ዋና ዋና ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ እንዲሁም ሌሎች ተያያዥ የሆኑ ነጥቦችን ያካተተ እንደሆነ ገልፀል፡፡
በሥልጠናው ላይ ከፍትሕ ሚኒስቴር እና ተጠሪ ተቋማት የተወጣጡ 80 ሴት አመራሮች የተሳተፉበት ሲሆን፣ ለሶስት ተከታታይ ቀናት በአፍሪካ አመራርነት ልህቀት አካዳሚ እንደተካሄደ ተገልፁዋል፡፡