የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ፍትሕ ሚኒስቴር ከሁሉም ክልሎች እና ተጠሪ ተቋማት ከተውጣጡ አመራሮች እና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ፎካል ፐርሰኖች ጋር በትራንፎርሜሽናል ዕቅድ፣ በ2016 በጀት ዓመት መሪ ዕቅድ እና በዕቅድ አዘገጃጀት ዙሪያ ሥልጠና መስጠት እና ውይይት ማድረግ ጀምሯል።
ውይይቱን በመልዕክታቸው ያስጀመሩት በፍትሕ ሚኒስቴር የተቋም ግንባታ እና ሪፎርም ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር ዶ/ር ኤርሚያስ የማነብርሀን እንደተናገሩት በሕገ-መንግስታችን እውቅና ካገኙ መርሆዎች መካከል አንዱ የሆነው የግልጸኝነት እና ተጠያቂነት መርህ እንደመሆኑ መጠን ተቋማቶቻችን የሚተገብሯቸውን ተግባራት በግልጽ ማቀድ እና በታቀደው መሠረት መፈጸም አለባቸው፤ ይህ ተጠያቂነትን ለማስፈን የራሱ የሆነ ሚና አለው ብለዋል።
ሚኒስትር ዴኤታው ንግግራቸውን ሲቀጥሉ የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድ ዝግጅቱ የትራንስፎርሜሽን ዕቅዱን ዓላማ እና ምሰሶዎችን ከግምት ያስገባ እንዲሆን በሀገር ዐቀፍ ደረጃ ወጥ የሆነ የፍትሕ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ዕቅድ ለማዘጋጀት ጉዳዩ ከሚመለከታቸው የፌዴራል እና ክልል የስራ ሀላፊዎች ጋር በዚህ መልኩ ውይይት ማድረጉ ለእቅዶቹ መሳካት ጉልህ ሚና ይጫወታል ብለዋል።
በመሆኑም በሥልጠናው እና በውይይቱ የሚገኙ ግብዓቶችን በሚገባ ቀምሮ በተቋሙ እቅድ ውስጥ በማካተት ለአፈጻጸሙ ውጤታማነት ከምታበረክቱት ሚና በተጓዳኝ ሀገር ዐቀፍ የፍትሕ ዘርፍ ሪፖርት መዘጋጀት ይችል ዘንድ ተግታችሁ ትሰሩ ዘንድ አደራ እላለው ብለዋል።
ንግግሩን ተከትሎ በፍትሕ ሚኒስቴር የፍትሕ ስርዐት ማሻሻያ እና ለውጥ አመራር ዳይሬክተር የሆኑት አቶ ኖህ ታከለ በትራንስፎርሜሽናል ፍትሕ ዕቅዱ ዙሪያ ገለጻ ያቀረቡ ሲሆን በአሁኑ ሰዐት በቀረበው ገለጻ ላይ ውይይት እየተደረገ ይገኛል።
ዉይይቱ ነገን ጨምሮ ለሁለት ቀናት የሚካሄድ ሲሆን የፍትሕ ሚኒስቴር የ2016 በጀት ዓመት መሪ ዕቅድም ቀርቦ ውይይት የሚካሄድ ይሆናል።