የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድን መሰረት በማድረግ በ2018 በጀት ዓመት 9ወራት ዕቅዶ የፈፀማቸውን ተግባራት የተቋሙ ከፍተኛ እና መካከለኛ አመራሮች በተገኙበት ሚያዚያ 9/2018 ዓ.ም ገምግሟል፡፡
በግምገማ መድረኩ የተሻሻለ የፍትሕ አገልግሎት ከመስጠት፤የሕግ የበላይነትን ከማጠናከር፤ የማረምና ማነፅ ሂደትን ከማሻሻል፤ ያደገ ተቋማዊ አቅምን ከመገንባት እንዲሁም ከፌደራልና ከክልል ተቋማት ጋር ያለን ቅንጅትና ትብብርን ከማጠናከር ጋር ተያይዞ በበጀት ዓመቱ የ9 ወራት ውስጥ ታቅደው ሲከናወኑ የቆዩ ተግባራት የተጠቃለለ ሪፖርት ቀርቧል፡፡
በዚህም በህሕ ማርቀቅ በኩል 11 ህጎች በዘጠኝ ወራት ውስጥ ማርቀቅ የተቻለ ሲሆን 164 ሕጎች ላይ የእርማት እንዲሁም 13 የሕግ ጥናቶች መካሄዳቸው በሪፖርቱ ተገለጿል ፤ በወንጀል አስተዳደር ውጤታማነት እና ቅልጥፍና አንፃር በፍትሕ ሚኒስቴር በሁሉም የወንጀል አይነቶች 34,548 የምርመራ መዝገቦች ውስጥ 34,329 መዝገቦች ላይ ዐቃቤ ሕግ የተለያዩ ውሳኔዎች መስጠቱ እንዲሁም በሁሉም ወንጀሎች በ33, 983 የክስ መዝገቦች ላይ ክርክር ተደርጎ 9,504 መዝገቦች ውሳኔ ያገኙ መሆናቸው ተገልጿል፡፡
በተጨማሪም ክልሎችን ጨምሮ በዘጠኝ ወራት ውስጥ በወንጀል የተገኘ ኃብት ከማስመለስ አንፃር 3,691,842,167 ብር 152,352 ካሬ ሜትር የከተማ እና 1,840.33 ካሬ የገጠር ቦታ በወንጀል የተገኘ ኃብትን በማስመለስ ለመንግስት ገቢ ማድረግ መቻሉ ተመላክቷል፡፡
በንቃተ ህግ ትምህርት በ147 ርዕሰ ጉዳዮች የተለያዩ ዘዴዎችን በመጠቀም 6 ሚሊየን ለሚገመት የሕብረተሰብ ክፍል የንቃተ ህግ ትምህርት መስጠት መቻሉ የተጠቆመ ሲሆን፣
የመንግስትና የህዝብ ፍትሐብሔራዊ ጥቅምን ከማክበርና ማስከበር፤ በሰብዓዊ መብት ማክበርና ማስከበር፤ የሕግ ተፈፃሚነትና ተገዥነት፤ በህገ ወጥ የሰዎች ዝውውር መከላከል፤የብሔራዊ ትብብር ጥምረትና በዓለም አቀፍ ትብብር በኩል በርካታ ተጨባጭና ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸው ተገልጿል፡፡
የቀረበውን ሪፖርት ተከትሎ ሰፊ ውይይት የተካሄደ ሲሆን፣ ባለፉት 9ወራት ተቋማዊ የትኩረት አቅጣጫ ሆነው የተቀመጡ ተግባራት ሲከናወኑ መቆየታቸው የተወሳ ሲሆን፣ ለአብነትም በመሰረተ ማህበረሰብ ፍትሕና የአማራጭ የሙግት መፍቻ አገልግሎትን በማስፋት፤ ከጥብቅና ፈቃድ ጋር የተያያዙ አገልግሎቶች በመሶብ አገልግሎት እንዲካተቱ ማድረግ መቻሉ፤ የምርመራ መዝገብ የማጥራት እና የወንጀል ክስ መርታት ምጣኔን ከማሳደግ ፤በወንጀል የተገኘ ሀብት ማስመለስ፤ በፍትሐብሔር ክስ(ቀጥታ ክስ፣በግልግል) ፤ የፌደራል ትብብርና ቅንጅትን በማጠናከር በተለይም የወንጀል ምርምራ፣ ክስ እና ክርክር ተግባራትን ውጤታማነት ለማሳደግ ከፌዴራል፣ ከአዲስ አበባ እና ከድሬዳዋ ፖሊስ ኮሚሽን የጋራ የአሰራር ስርዓት እና የጋራ ዕድቅ በማዘጋጀት ተግባራዊ ማድረግ መቻሉ ከተገኙ ስኬቶች መካከል ተጠቃሽ ናቸው፡፡