የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. የፍትሕ ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ጋር በመተባበር የሁሉንም ዓይነት አድሏዊ የዘር ልዩነቶችን ለማስወገድ በተደረገ ዓለም አቀፍ ስምምነት (Convention on the Elimination of Racial Discrmination) የተጠቃለለ ወቅታዊ አገራዊ የአፈፃፀም ረቂቅ ሪፖርት ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ሰኔ 5/2018 ዓ.ም ውይይት አካሂዷል፡፡
አገራዊ የአፈጻፀም ሪፖርት ማዘጋጀት በስምምነቱ መሰረት የግል ግምገማ ለማካሄድ፣ ዓለም አቀፍ ግዴታን ለመወጣት፣ በሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተሳትፎ ለማድረግ፣ ትክክለኛውን የአገሪቱን የስብአዊ መብት ገፅታ ለዓለም አቀፉ ህብረተሰብ ለማስገንዘብ፣ አገራዊ ምክክርን ለማጎልበት፣ ከልማት አጋሮች ጋር በትብብር ለመስራት፣ የዓለም አቀፍ ባለሙያዎችን ምክክር እንዲሁም የተለያዩ አገራትን ለምድ ለማግኘት እና ችግሮችን ለመለየት የራሱ የሆነ ፋይዳ እንዳለው ተገልጿል፡፡
በውይይቱ ወቅት በተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ ሥርዓት ውስጥ የዘር መድሎን መከላከል አንደኛውና ዋነኛው መሠረት መሆኑ የተወሳ ሲሆን፣ ይህንን የመብት ጥሰት በሁሉም ደረጃ ለመከላከልና ኢትዮጵያ የተቀበለቻቸውን ስምምነቶች በማክበርና በማስከበር ረገድ መንግሥት የበኩሉን ኃላፊነት እየተወጣ እንደሚገኝ በመጠቆም፡ ይህንን አገር አቀፍ የአፈጻፀም ሪፖርት ምሉዕ፣ ወቅታዊና ተዓማኒ ለማድረግም መንግሥታዊ አካላት እና መንግስታዊ ያልሆኑ የሲቪል ማኅበረሰብ ተቋማት መረጃዎችንና ሙያዊ ምክረ-ሐሳቦችን በግብዓትነት በማቅረብ የሚጠበቅባቸውን አገራዊ ኃላፊነት እንዲወጡ ጥሪ ቀርቧል።
የመድረኩ ተሳታፊዎች በስምምነቱ መሠረት የፈራሚ አገራትን ዋና ዋና ግዴታዎች በስፋት የዳሰሱ ሲሆን ፈራሚ አገራት የዘር መድሎ ድርጊቶችን በቀጥታ ከመፈጸም መቆጠብ፣ በሌሎች አካላት እንዳይፈጸም የመከላከልና የቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋት፣ እንዲሁም ለጥሰቱ ተጋላጭ የሆኑ የኅብረተሰብ ክፍሎችን በልዩ ሁኔታ የመጠበቅ ኃላፊነት እንዳለባቸው በማብራራት ሰብዓዊ መብቶችን የሚያስከብሩ ተቋማትን ማጠናከርና በዘር ላይ የተመሠረቱ ማናቸውንም ዓይነት የጥላቻ ቅስቀሳዎችን በሕግ መከላከል የስምምነቱ መሠረታዊ ጉዳዮች መሆናቸው ተገልጿል።
በመጨረሻም ቀደም ሲል ከኢትዮጵያ ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ቀርቦ ከነበረው የአፈጻጸም ሪፖርት የተገኙ ግብረ-መልሶችንና ምክረ-ሃሳቦችን እንዲሁም ወቅታዊውን የአገሪቱን ተጨባጭ ሁኔታ መሠረት በማድረግ በተዘጋጀው በዚህ ረቂቅ የአፈጻፀም ሪፖርት ላይ ሰፊ ውይይት የተደረገ ሲሆን ከተሳታፊዎች የተሰበሰቡ ጠቃሚ አሳቦችና ገንቢ አስተያቶች በግብዓትነት ተይዘው እንዲሁም ቀጣይ ሥራዎች ተመላክተው ውይይቱ ተጠናቋል።