ፍትሕ ሚኒስቴር ከእስር ውጭ ያሉ አማራጭ የመፍትሔ እርምጃዎች የአፈጻጸም ስነስርዓት ረቂቅ ደንብ እና አማራጭ የመፍትሔ እርምጃዎች አስፈፃሚ አካላት ማቋቋሚያ ረቂቅ ደንብን በማጥናት እርምጃዎችን ለማስቀመጥ ያለመ ጥናት ላይ ከፍትሕ አካላት ጋር በሸራተን ሆቴል ውይይት አድርጓል፡፡
የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የመንግሥት ሕግና ፍትሕ አገልግልት ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ ክቡር አቶ በላይሁን ይርጋ በመድረክ መክፈቻ ንግግራቸው በኢትዮጵያ የፍትሕ አስተዳደር ስርዓት ውስጥ እንደክፍተት ከሚታዩ ጉዳዮች አንዱ አማራጭ የቅጣት ማስፈፀሚያ መንገዶች መፍትሔ ያለመኖሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ክቡር ሚኒስትር ዴኤታው አያይዘውም Substantive እና procedural ህጎች አማራጭ የቅጣት ማስፈፀሚያ መንገዶችን ይፈቅዳሉ ወደተግባር ሲገባ ግን ብዙ ክፍተቶች ይስተዋላሉ ብለዋል፡፡
አክለውም ፍትሕ ሚኒስቴር ከፍትሕ አካላት ጋር በመሆን የሕግ ታራሚዎችን ከማረም ፣ከማነጽ እና ከመቀላቀል ጋር ያሉ ክፍተቶችን በመሙላት የተሻለ ለውጥ እንደሚያስመዘግብ አመላክተዋል፡፡
በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የሴቶችና ባለብዙ ዘርፍ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወ/ሮ ዳግማዊት አላምኔ በበኩላቸው ከእስር ውጭ ያሉ አማራጭ የቅጣት ውሳኔዎች አተገባበርን በተመለከተ የተዘረጉ አሰራሮች እንዲሁም አፈፃፀማቸው ወጥነት የሌላቸው መሆኑ በየጊዜው በሚያጋጥሙ ጉዳዮች የሚታወቁ መሆናቸውን ገልጸው የዚህንም አሠራር ለመዘርጋት እንዲሁም አፈጻጸሙን ለመከታተል የሚያስችሉ ረቂቅ ደንቦች በፍትሕ ሚኒስቴር መዘጋጀታቸውን የጠቆሙት ዳግማዊት የዛሬው መድረክ ዓላማም በሚቀርቡ ረቂቅ ደንቦች ላይ ግብኣት ለማሰባሰብ ያለመ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የወንጀል ስነስርዓትና ማስረጃ ሕግ ፕሮጀክት ማስተባበሪያ ፅህፈት ቤት ኃላፊ ወ/ሮ ትዕግስት መሀቤ የወጣቶች ስብህና መገንቢያ ማዕከላትን ማስፋፋት ወጣቶች ወደአዕምሮ ህክምና ማሕከልና ወደማረሚያ ቤት የሚመላለሱበትን ሁኔታ እንደሚቀንስ አውስተው የዚህ ደንብ መፅደቅ ለወንጀል ስነስርዓት ህጉ መፅደቅ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል፡፡
ረቂቅ ደንቦቹ ከፍትሕ ሚኒስቴር ጋር በመሆን በማርቀቅ ሂደት ዕገዛ ሲደርጉ በነበሩት የሕግ አማካሪ በአቶ ደቻሳ እና ሚልኪ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበት ከተሳታፊዎች ጥያቄና አስተያየት ቀርበው ማብራሪያና ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡