ጌታቸው አለምፀሀይ የተባለው ተከሳሽ የስራ ባልደረባው የነበረችውን የፍቅር ጥያቄ አቅርቦላት ባለትዳር ነኝ በማለቷ በስራ ገበታዋ ላይ እያለች እያባረረ በቢላዋ በመውጋት ህይወቷ እንዲልፍ አድርጎ በሌለበት በእድሜ ልክ ጽኑ እስራት ተቀጥቷል፡፡
በዐቃቤ ሕግ የክስ መዝገብ ላይ ተከሳሹ ሰውን ለመግደል አስቀድሞ በነበረው ሀሳብ ጥር 2 ቀን 2011 ዓ.ም በግምት ከረፋዱ 5፡30 ሰዓት ሲሆን በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 02 ሳባ ህንፃ 6ኛ ፎቅ ላይ የስራ ባልደረባው የነበረችውን ሟች ወ/ሮ መዓዛ ካሳን የፍቅር ጥያቄ አቅርቦላት ባለትዳር ነኝ ስትለው የግድ አብረን እንሁን እያለ ሲያስቸግራት ቆይቶ ፈቃደኛ ባለመሆኗ በስራ ገበታዋ ላይ እያለች ጨካኝነቱን እና ነውረኝነቱን በሚያሳይ መልኩ እያባረረ በቢላዋ በመውጋት በደረሰባት ጉዳት ወደ ሆስፒታል ከተወሰደች በኋላ የህክምና እርዳታ ሲደረግላት ቆይቶ ጉዳቷ በመባባሱ ህይወቷ ያለፈ በመሆኑ በፍትሕ ሚኒስቴር የጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ዘርፍ በሴቶችና ህጻናት ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎች ዐቃቤ ሕግ ዳይሬክቶሬት በፌዴራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 1ኛ የሰው ግድያና ከባድ ውንብድና ወንጀል ችሎት ክስ አቅርቦበት ክርክር ተደርጎ በተከሳሽ ላይ የጥፋተኛነት ፍርድ በመስጠት፣ ነሐሴ 4 ቀን 2014 ዓ.ም በዋለው ችሎት በዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት የተቀጣና ህዝባዊ መብቶቹ ለዘወትር እንዲሻሩ በሌለበት ተወስኖበት የነበረ መሆኑን በፌስ ቡክ ገፃችን ማጋራታችን ይታወሳል፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ግለሰቡን ሲያፈላልግ ቆይቶ መጋቢት 21 ቀን 2017 ዓ.ም ከተሸሸገበት በመያዝ በሕግ ጥላ ስር ሆኖ የእስራት ቅጣቱን እንዲፈፅም ወደ ማረሚያ ቤት እንዲላክ አድርጓል፡፡