በግል የሚሰሩ ጠበቆች እና የጥብቅና ድርጅቶች የግብር አከፋፈል በተለይ የሒሳብ መዝገብ አያያዝ እና የወጪ አመዘጋገብ ጋር በተገናኘ የሚስተዋሉ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት የሚያስችል ውይይት ከፍትሕ ሚኒስቴር፣ ከገንዘብ ሚኒስቴር፣ ከአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ እና ከፌደራል ጠበቆች ማህበር ጉዳዩ የሚመለከታቸው ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች በተገኙበት በሚያዚያ 18 ቀን 2016 ዓ.ም ውይይት ተካሄዷል፡፡
የፍትሕ ሚኒስቴር የመንግሥት ሕግና ፍትሕ አገልግሎት ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ ክቡር አቶ በላይሁን ይርጋ በጠበቆች እና የጥብቅና ድርጅቶች የግብር አከፋፈል ላይ የሚነሱ የሕግ እና የአሠራር ክፍተቶችን ለመቅረፍ ከዚህ ቀደም የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት ጥናት መከናወኑን እና በጥናቱ የተመላከቱ የመፍትሔ ሀሳቦችን መሠረት በማድረግ የተከናወኑ ተግባራት መኖራቸውን አስታውሰው ቀጣይ ተግባራት ላይ ለመወያየት ይህ የውይይት መድረክ መዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡
በውይይት መድረኩ ላይ የጥናት ሰነዱ ቀርቦ ውይይት የተደረገበት ሲሆን በጥብቅና ሙያ ሥራ ግብር አከፋፈል ላይ በተለይ የሂሳብ መዝገብ እና የወጪ አያያዝ ጋር በተገናኘ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ ከበጀት ዓመቱ የግብር መክፍያ ወቅት በፊት ቅደሚያ ተስጥቷቸው ሊከናወኑ የሚገቡ ተግባራት የተለዩ ሲሆን በቅንጅት ለመሥራት ከመግባባት ላይ ተደርሶ ውይይቱ ተጠናቋል፡፡