የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር ከUNODC ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው እና ትኩረቱን የወንጀል ሥጋትን አስመልክቶ በተከናወነ የዳሰሳ ጥናት ላይ ያደረገ የውይይት መድረክ ታህሳስ 9/2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ተካሂዷል፡፡
በመድረኩ በሀገር አቀፍ የወንጀል መከላከል ስትራቴጅ አፈጻጸም ዙሪያ የተለያዩ አገራት ተሞክሮ የቀረበ ሲሆን፤ ወንጀል መከላከል የመንግሥታት ዋነኛ የፖሊሲ አካል መሆኑ፤የወንጀል መከላከል ስትራቴጂዎችንና ፕሮግራሞችን መቅረጽ እና ሁሉን ዓቀፍ ወንጀል መከላከልን ተግባራዊ ማድረግ አንዱ ሲሆን፤ ሕብረተሰቡን ያሳተፈ የወንጀል መከላከል ሥራን ተግባራዊ ማድረግ ውጤታማ እንደሚሆን ተመላክቷል፡፡
በአዲስ አበባ ከተማ በተመረጡ ክፍለከተሞች ላይ ያተኮረ የወንጀል ሥጋት የዳሰሳ ጥናት የቀረበ ቀርቧል፡፡ በዳሰሳ ጥናቱ የሚፈጸሙ የወንጀል አይነቶች፤ባህሪያት፤ደረጃዎች እና ወንጀሉ የሚፈጸምበት ጊዜ ለመድረኩ ተሳታፊዎች የጥናት ግኝቱን መሠረት በማድረግ ገለጻ በማቅረብ ሰፋ ያለ ውይይት ተካሂዱዋል፡፡
የዉይይት መድረኩ ያስፈለገዉ በተለያዩ አገራት ወንጀል መከላከል ላይ የተሠሩ ምርጥ ተሞክሮዎችን ለአመራሮቹ በማስገንዘብ እና ይህን መሰል ጥናት ተጠናክሮ ቢቀጥል ወንጀል ከመፈፀሙ በፊት አስቀድሞ ለመከላከል የራሱ የሆነ አስተዋፅዖ እንደሚኖረው እና በቀጣይ ሀገር አቀፍ የወንጀል መከላከል ስትራቴጅን ለማስተግበር የሚመለከታቸው ተቋማት በቅንጅት መስራት የሚጠበቅባቸው መሆኑን መነቃቃትን ለመፍጠር እንደሆነም ተገልጿል፡፡
በውይይት መድረኩ ፍትሕ ሚኒስቴርን ጨምሮ የፌደራል እንዲሁም የክልል የፍትሕ አካላት እና ከተለያዩ የመንግሥት ባለድርሻ ተቋማት የተወጣጡ ከፍተኛ እና መካከለኛ አመራሮች ተሳትፈውበታል፡፡