የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር “ሠንደቅ ዓላማችን ለኢትዮጵያ ታላቅ የከፍታ ዘመን ብሥራት፣ ለብሔራዊ አንድነታችን፣ ለሉዓላዊነታችንና ለኢትዮጵያ ሕዳሴ!” በሚል መሪ ቃል በዛሬዉ እለት በመላው አገሪቱ ተከብሮ የሚዉለዉን 18ኛዉን የሠንደቅ ዓላማ ቀን የተቋሙ ከፍተኛ እና መካከለኛ አመራሮች ብሎም ሰራተኞች በተገኙበት አክብሯል፡፡
የኢትዮጵያዊነት የማንነት ዓርማና መገለጫ የሆነዉ የብሔራዊ የሠንደቅ ዓላማ ቀን በሠንደቅ ዓላማ አዋጅ 863/2006 አንቀጽ 2 መሰረት በየዓመቱ ጥቅምት ወር በገባ በመጀመሪያዉ ሳምንት ሰኞ ዕለት እንደሚከበር የሚደነግግ ሲሆን ይህንኑ ተከትሎ በዛሬዉ እለት በዓሉ ተከብሮ ዉሏል፡፡
በዓሉ የሚከበርበት ዋና ዓላማም ለሠንደቅ ዓላማ የሚገባዉን ክብር በመስጠት ዜጎች የጋራ ዕሴቶቻቸዉን የሚያጠናክሩበትና በአገራዊ አንድነትና ኅብረ -ብሔራዊነት መግባባትን የሚፈጥሩበት አገራዊ በዓል መሆኑ ሲሆን ዘንድሮ ለ18ኛ ጊዜ በዓሉ ሲከበር የኢትየጵያዉያን ብሔራዊ ጥቅም ማሳያ የሆነዉ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ተመርቆ ስራ በጀመረበት ማግስት መሆኑ ለየት እንደሚያደርገዉም ተመላክቷል፡፡
በመጨረሻም የተቋሙ አመራርና ሰራተኞች በሠንደቅ ዓላማ ፊት ቆመዉ ቃለ መሀላ በመፈፀም ለአገራቸዉና ለሠንደቅ ዓላማቸዉ ያላቸዉን ክብርና ፍቅር ዳግም በመግለፅ የአገራቸዉን አንድነትና ሉአላዊነት ለማስጠበቅ ቃላቸዉን አድሰዋል፡፡