የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ሰራተኞች እና የተጠሪ ተቋማት ሰራተኞች የብሔራዊ ዲጅታል መታወቂያ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማድረግ በዛሬው እለት በፍትሕ ሚኒስቴር ምዝገባ መጀመሩን በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የመንግሥት ሕግና ፍትሕ አገልግሎት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ በላይሁን ይርጋ አሳወቁ፡፡
በፍትሕ ሚኒስቴር የተቋም ግንባታ እና ሪፎርም ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ኤርሚያስ የማነብርሃን በዛሬው እለት ተመዝግበዋል፡፡
በፍትሕ ሚኒስቴር ለአገልግሎት የሚመጡ ተገልጋዮች የብሔራዊ ዲጅታል መታወቂያ ተጠቃሚ ለመሆን መመዝገብ እንደሚችሉ ሚኒስቴር ዴኤታው የጠቆሙ ሲሆን የተቋሙና የተጠሪ ተቋማት ሰራተኞች እንዲሁም ጠበቆች ተመዝግበው እስከሚጨርሱ ድረስ ምዝገባው እንደሚቀጥል ተገልጿል፡፡
በፍትሕ ሚኒስቴር የሚሰጡ አገልግሎቶች በብሔራዊ ዲጅታል መታወቂያ ብቻ እንዲሆኑ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ ስለመሆኑ እና ፍትሕ ሚኒስቴር ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ሙሉ ለሙሉ አገልግሎቱን ወደ ብሔራዊ ዲጅታል መታወቂያ ስለሚቀይር አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት መደረግ እንዳለበት ሚኒስትር ዴኤታው ማሳሰባቸውን ከአሁን በፊት መዘገባችን ይታወሳል፡፡
በዛሬዉ እለት በተቋሙ በተጀመረው የብሔራዊ ዲጅታል መታወቂያ ምዝገባም ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ኤርሚያስ የማነብርሃን እና የተቋሙ ሰራተኞች እና ጠበቆች እየተመዘገቡ ይገኛል፡፡