በሰው መነገድ እና በህገወጥ መንገድ ድንበር ማሻገር ወንጀሎች በዜጎች አካል እና ደኅንነት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሱና ለሰብዓዊ መብት የሚያጋልጡ ከመሆናቸውም በላይ በሀገር ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሚያደርሱ መሆናቸውንና ወንጀሉን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የተጎጅ ምስክሮች ተሳትፎ እጅግ ወሳኝ ቢሆንም ለተጎጅ ምስክሮች የሚደረግ የተጠናከረ ጥበቃና ድጋፍ ባለመኖሩ ምክንያት ብዙ ተጎጅ ምስክሮች ለምስክርነት ለመቅረብ ፍላጎት እንደሌላቸው ይህም ወንጀል አድራጊዎችን ወደ ፍትሕ ከማቅረብ አንጻር አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩን እና የመግባቢያ ሰነዱ በሕግ አስፈጻሚ አካላትና በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት መካከል ያለውን ትብብር በማሳደግ ተጎጅ ምስክሮች የሚሰጣቸው ድጋፍ ሁሉን አቀፍ በሆነ መልኩ የሚያሳድግ እና በምርመራ እና በፍርድ ሂደት ደህንነታቸው ተጠብቆ ውጤታማ ተሳትፎ እንዲያደርጉ የሚያስችል መሆኑን በፍትሕ ሚኒስቴር የጠቅላይ ዐ/ሕግ ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ የሆኑት ክቡር አቶ ፍቃዱ ፀጋ ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል ዘላለም መንግስቴ በበኩላቸው ይህ የመግባቢያ ሰነድ መፈረሙ ወንጀሎቹን ከመከላከል እና ከመቆጣጠር አንጻር ብሎም የተጎጂዎችን መብት ከማስከበር አንጻር ከፍተኛ አስተዋጾ እንደሚኖረው እና ተመሳሳይ ተሞክሮ ወደ ክልሎችም መስፋፋት እንዳለበት ገልጸዋል፡፡
የመግባቢያ ሰነዱን የፈረሙት አገልግሎት ሰጪ የሆኑት ተቋማትም በመግባቢያ ሰነዱ መሠረት ተደራሽ ወጥ እና ፍትሃዊ የሆነ አገልግሎት መስጠታቸውን እና ከሕግ አስከባሪ ተቋማት ጋር በትብብር መስራታቸውን እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል፡፡
በመጨረሻም ክቡር አቶ ፈቃዱ ጸጋ የመግባቢያ ሰነዱን አተገባበር እና አፈጻጸምን በተመለከተ እያንዳንዱ ፈራሚ ተቋም በትጋት እና በትብብር መሥራት እንዳለበት እንዲሁም የፍልሰት ብሔራዊ የትብብር ጥምረት ፅ/ቤት የመግባቢያ ሰነዱ እንዲተገበር የማስተባበር ኃላፊነቱን እንዲወጣ በማሳሰብ የማጠቃለያ ሀሳብ ሰጥተዋል፡፡