በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ዘርፍ የኢኮኖሚ ወንጀል ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዐቃቤ ሕግ አሸናፊ ተሰማ በተባለው ተከሳሽ ላይ በፈጸመው የኮንትሮባንድ ወንጀል በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የልደታ ምድብ 9ኛ የወንጀል ችሎት በዛሬው ዕለት ክስ መሰረተ፡፡
የወንጀል አፈጻጸሙን በተመለከተ የዐቃቤ ሕግ የክስ መዝገብ እንደሚያመላክተው ተከሳሽ ተገቢው የጉምሩክ ሥነ-ሥርዓት ያልተፈፀመባቸው ዕቃዎች መሆናቸውን እያወቀ ወይም ማወቅ ሲገባው የዋጋ ግምታቸው 11 ሚሊዮን 910 ሺ ብር የሚያወጡ በቁጥር 970 ሞባይሎችን እና ብር 3, ሚሊዮን 222ሺ ብር የሚያወጡ 17.9 ኪ.ግ የሚመዝኑ የብር ጌጣጌጦችን በድምሩ 15 ሚሊዮን 132 ሺ ብር የሚያወጡ ህገ-ወጥ ዕቃዎችን በመኪና ጭኖ ሲያጓጉዝ አዲስ አበባ ከተማ አዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 08 ልዩ ቦታው አዲስ አበባ የገበያ ማዕከል አካባቢ በቀን ሰኔ 15 ቀን/2015 ዓ.ም በግምት ከረፋዱ 5፡00 ሰዓት የተያዘ በመሆኑ የጉምሩክ አዋጅ አዋጅ ቁጥር 859/2006 [በጉምሩክ አዋጅ (ማሻሻያ) አዋጅ ቁጥር 1160/2011 እንደተሻሻለው] አንቀጽ 168(2) ስር የተደነገገውን ድንጋጌ በመተላለፍ በፈፀመው በህገ-ወጥ መንገድ ወደ አገር ውስጥ የገባን ዕቃ ማጓጓዝ የኮንትሮባንድ ወንጀል ተከሷል፡፡
ጉዳዩን የተመለከተው ችሎትም ተከሳሽ ያቀረበውን የክስ መቃወሚያ ውድቅ በማድረግ የእምነት ክህደት ቃሉን እንዲሰጥ በማድረግ ክዶ የተከራከረ በመሆኑ የዐቃቤ ሕግን ማስረጃ ለመስማት ለሀምሌ 15/2015 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡