በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የክልል ጉዳዮች ክትትል እና ድጋፍ ዳይሬክቶሬት አሰተባባሪነት ከትላንት ጀምሮ በአዳማ ከተማ ሲካሄድ የነበረው የክልል ፍትሕ ቢሮዎች የ2017 በጀት ዓመት የ9ወራት የመደበኛ እና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ አፈፃፀም የውይይት መድረክ ተጠናቀቀ፡፡
የውይይት መድረኩ በዛሬ ውሎው የፌደራል ወንጀል ጉዳይ የስረ-ነገር ሥልጣንን በተመለከተ በተለይም የክልልና የፌደራል ህገ-መንግሥት መኖር ጥቅሞች፤የመንግሥት የሥልጣን አካላት አወቃቀር፤ የፌደራል መንግሥት እና የክልል መንግስታት ግንኙነት (የፌደራል ህጎችን ከማስፈፀም አንፃር)፤ የወንጀል ሕግን የማስፈፀም ሥልጣን፤ የፍትሕ ሚኒስቴር ሥልጣንና ተግባር ላይ ያተኮረ የውይይት መነሻ ሰነድ በፍትሕ ሚኒስቴር የሚኒስትር አማካሪ በሆኑት አቶ ገብሩ ገበየሁ አማኝነት ቀርቧል፡፡
ቀጥሎም በሽግግር ፍትሕ ትግበራ ሂደት የፍትሕ ሚኒስቴር ሚና ምን እንደሆነ፤ የሽግግር ፍትሕ ፓሊሲ ይዘት፤የፓሊሲውን መፅደቅ ተከትሎ የተሰሩ ስራዎችና ቀጣይ ተግባራት እንዲሁም በቀጣይ ሂደቶች የክልሎች ሚናን በተመለከተ በፍትሕ ሚኒስቴር የስብአዊ መብት ዲርጊት መርሀ-ግር ዳይሬክቶሬት ዐ/ሕግ በሆኑት አቶ አሰፋው አንሳቦ አማካኝነት ለተሳታፊዎች ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡
በመጨረሻም ትላትናን ጨምሮ በዛሬው ዕለት በቀረቡ ሪፖርቶች እና የውይይት መነሻ ሰነዶች ላይ ሃሳብ አሰተያየቶች እንዲሁም ጥያቄዎች ቀርበው ሰፋ ያለ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
በፍትሕ ሚኒስቴር የተቋም ግንበታና ሪፎርም ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር ዶ/ር ኤርምያስ የማነብርሃን በውይይት መድረኩ ማጠቃላያ ላይ እንደተናገሩት የመድረኩ ተሳታፊዎች በቀጣይ ከመድረኩ ያገኙትን ግብአት ለሚመለከታቸው አካላት በማስገንዘብ እንዲሁም በመገምገም የዕቅድና ሪፖርት አካል እንዲሆኑ በማድረግ በጥራት፤ በውጤት ፤በይዘት የተሻለ እና ተአማኒነት ያለው ፤ የጠራ እና የተናበበ ሪፖርት መረጃ እንዲያዝ በማድረግ የወንጀል ፍትሕ ሥርዓት የማሻሻል ስራውን ለማገዝ የበኩላቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ አሳስበው፣ ፍትሕ ሚኒስቴርም በዚህ ረገድ አሰፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ በመግለፅ እና ቀጠይ አቅጣጫዎችን በመስጠት የውይይት መድረኩ ተጠናቋል፡፡