በኢ.ፌ.ደ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የጠቅላይ ዐቃቤ ህግ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አቶ ቸርነት ሆርዶፋ የተመራ ልዑክ በፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ በመገኘት እየተከናወኑ የሚገኙ የሪፎርም ስራዎች በተገኙ ውጤቶች ላይ ከፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ አመራሮች ጋር ውይይት አካሂዷል፡፡
በውይይቱ የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ ኃላፊ ተወካይ ክቡር አቶ ሙሊሳ አብዲሳ እንዲሁም በየደረጃው የሚገኙ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡
በስራ ጉብኝት እና ውይይት ወቅት በፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ በኩል የተከናወኑ የፎርም ስራዎች እና የተገኙ ውጤቶች ሪፖርት የቀረቡ ሲሆን፣ በተከናወኑ የሪፎርም ስራ የወንጀል ምርመራ ስራዎች በሳይንሳዊ መንገድ በመምራት በሀገር ደህንነት እና በሕዝብ ጥቅም ላይ የተፈፀሙ ወንጀሎችን ከዐቃቤ ህግ ጋር በመቀናጀት ምርመራ በማከናወን አጥፊዎችን ተጠያቂ የማድረግ ውጤታማ ስራዎች የተሰሩ መሆኑ ተገልጿል፡፡
የፌዴራል ፖሊስ ባከናወናቸው የሪፎርም ስራዎች የሕግ የበላይነት ከማስከበር ረገድ አበረታች ውጤቶች የተገኙ በመሆኑ ይህን የተገኘ ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል ፖሊስና ዐቃቤ ህግ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ በቅንጅት በመስራት የህግ የበላይነትን የማስከበር እና ተቋማቱ በሕዝብ ዕምነት የሚጣልባቸው የማድረግ ስራዎችን የማከናወን እንደሚገባ ክቡር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ቸርነት ሆርዶፋ ገልፀዋል፡፡