የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ የሰው ሀብት አስተዳደር ስርዓቱን ውጤታማ ለማድረግ፣ በየጊዜው ወቅቱን የሚመጥን የማሻሻያ ስራ ለማከናወን፣ ብልሹ አሠራርን ለማስወገድ፣ የሰራተኞችን ተነሳሽነት ለማሳደግ፣ ሰራተኞችን ለመሳብና ለማቆየት እና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ዋነኛው የሪፎርም አካል መሆኑን ግምት ውስጥ በማስገባት ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት ላይ ይገኛል፤
በዚህም መሠረት የሰው ሀብት ስምሪት አይነት ከሆኑት መካከል የዝውውር አሠራር አንዱ በመሆኑ የግልጸኝነትና ተጠያቂነት አሠራርን ለማስፈን በሚደረገው እንቅስቃሴ ትኩረት የተሰጠው የስምሪት አይነት በመሆኑ ከሌሎች መመሪያዎች ጋር በየደረጃው የሚገኙ የሰው ሀብት ስራ አመራር ባለሙያዎችና የሚመለከታቸው ከአስተዳደሩ ውጪ የሆኑ ባለድርሻ አካላት ጭምር ውይይትና ተሳትፎ ካደረጉበት በኋላ የተለያዩ ግብዓቶችን በማሰባሰብ ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ በስራ ላይ የቆየውን የዝውውር አፈፃፀም መመሪያ በማሻሻል በመንግሥት ሠራተኛ አዋጅ 56/2010 በአንቀጽ 97 ንዑስ አንቀጽ 2 መሠረት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ይህንን የመንግሥት ሠራተኞች የተሻሻለውን የዝውውር አፈፃፀም መመሪያ አውጥቷል፡፡