የ1954 የወንጀል ሥነ ሥርዓት ሕጉ ለበርካታ አሥርት ዓመታት በሥራ ላይ የቆየ በመሆኑ ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ሕገ መንግሥት፣ በ1997 ከወጣው የወንጀል ሕግ፣ ሀገራችን ከምትተገብረው የወንጀል ፍትሕ ፖሊሲ እንዲሁም በዓለም ዓቀፍ ደረጃ በዘርፉ ካሉ አዳዲስ አሠራሮችና የቴክኖሎጂ እድገቶች አኳያ ከዘመኑ ጋር በተጣጣመ መልኩ መከለሱ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ባለፉት ዓመታት የአዲስ ሕግ ዝግጅት ሲደረግ ቆይቷል። ዛሬ የጸደቀው የሕግ መድብል አዳዲስ አሠራሮችን ከማስተዋወቁ በተጨማሪ የማስረጃ ሕግ በማካተት በኢትዮጵያ የወንጀል ፍትሕ ሥርዓት ውስጥ የቆየውን አንድ ትልቅ ክፍተት ለመሙላት አስችሏል። ሕጉ የወንጀል ምርመራ፣ ክስና ማስረጃ ሥርዓቱን ወደአዲስ ምዕራፍ የሚያሸጋግር ነው።
የወንጀል ሥነ ሥርዓትና ማስረጃ ሕጉ በማርቀቅ ሂደት ከ15 ዓመታት በላይ የወሰደ ሲሆን ባለፉት የለውጥ ዓመታት ከተለዩ ቁልፍ የሕግ ሪፎርሞች አንዱ ሆኖ፣ ብዙ ምክክር ተደርጎበት ሊጸድቅ ችሏል። ሕጉ ሀገር አቀፍ ተፈጻሚነት ያለው ሲሆን ከዚህ ሪፎርም የሚጠበቀውን ውጤት እውን ለማድረግ የፍትሕ ሚኒስቴር በሁሉም ደረጃ ከሚገኙ የፍትሕ አካላት ጋር በቅንጅት ይሠራል።