ቀን: ግንቦት 2014 ዓ.ም.
ንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር
Ministry of Trade and Regional Integration

በንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር የፌዴራል አስተዳደር ሥነ-ሥርዓት አዋጅ ቁጥር 1183/2012 ዓ.ም አፈፃፀም

በሀገራችን የአስተዳደር ሥነ-ሥርዓት ዓዋጅ ጸድቆ በቅርቡ ሥራ ላይ እንደዋለ ይታወቃል። ይህ አዋጅ የአስተዳደር ተቋማት በሕግ በተሰጣቸው መመሪያ የማውጣት ስልጣንና ባላቸው ከፊል የዳኝነት ስልጣን መሰረት በዕለት ተዕለት ተግባራቸው ውሳኔ በሚያስተላልፉበት ጊዜ የዘፈቀደ አሰራር እንዳይኖር እና የተገልጋዮች መብት ያለአግባብ እንዳይጣስ ለመከላከል ያለመ ነው። ይህ የክትትል ሪፖርት በንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር የአስተዳደር ሥነ-ሥርዓት አዋጅ አፈጻጸምን የሚዳስስ ነው።

የመረጃ አሰባሰብ ዘዴ

ለዚህ ጥናት የመረጃ አሰባሰብ ዘዴ የመጀመሪያ የመረጃ ምንጭ የሆኑትን የሕግ ዳሰሳዎች ያካትታል። ይህም ተቋሙ በአዋጅ 1263/2014 እና በሌሎች ሕጎች የተሰጡትን ስልጣንና ተግባራት መፈተሽ ነው። በተጨማሪም ከመመሪያ አወጣጥና አስተዳደራዊ ውሳኔ አሰጣጥ ጋር ግንኙነት ያላቸውን የስራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎችን ቃለ-መጠይቅና ውይይቶች በማድረግ እንዲሁም በምልከታ መረጃዎች ተሰብስበዋል። እንደ ሁለተኛ የመረጃ ምንጭ ደግሞ በተቋሙ የተሰጡ አስተዳደራዊ ውሳኔዎች እንደ ሰነድ ማስረጃ ተጠቅመዋል።

የሪፖርቱ ዋና ዋና ግኝቶች

1. ከመመሪያ አወጣጥና ምዝገባ ጋር በተያያዘ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የተጠሪ ተቋማትን ጨምሮ 41 መመሪያዎችን በፍትህ ሚኒስቴር ማስመዝገቡ፣ እንዲሁም ከመመሪያ ተደራሽነት አንጻር በከፊልም ቢሆን በድረ-ገጽ ላይ የመጫን ተግባር ማከናወኑ እና ረቂቅ መመሪያዎችን ለአስተያየት ወደ ፍትህ ሚኒስቴር የመላክ አሰራር መጀመሩ አዎንታዊ ነው።

ሆኖም ግን፣ አሉታዊ ጎኖቹ የሚከተሉትን ያካትታሉ፡-

  • ነባር መመሪያዎች፣ ማኑዋሎችና ሰርኩላሮች ያልተመዘገቡ መኖራቸው።
  • የአዲስ መመሪያዎች አወጣጥ ሂደት በአዋጁ መሰረት ያልተደራጀ መዝገብ አለመኖር።
  • ከህብረተሰቡ አስተያየት ለመሰብሰብ ማስታወቂያ አለማውጣት።
  • ለባለድርሻ አካላትና ለሚመለከታቸው የመንግስት ተቋማት ረቂቅ መመሪያ አለመላክ።
  • ክፍት የውይይት መድረክ አለማዘጋጀት።
  • የመመሪያዎች ማብራሪያ አለመኖር።
  • የወጡ መመሪያዎችን ሙሉ በሙሉ በድረ-ገጽ ላይ ተደራሽ አለማድረግ።

2. ከአስተዳደራዊ ውሳኔ አሰጣጥና ቅሬታ አቀራረብ ጋር በተያያዘ የአስተዳደር ውሳኔ ይሰጠኝ አቤቱታ በጽሁፍ እንዲቀርብ የሚያስችሉ ቅጾች መኖራቸው፣ ተገልጋዮች የሚያቀርቡት የሰነድ ማስረጃ የመመልከት አሰራር መኖሩ፣ እንዲሁም የአስተዳደር ውሳኔ በጽሁፍ ለተገልጋዩ የመስጠትና ቅሬታ ተቀብሎ የማስተናገድ አሰራር መኖሩ አዎንታዊ ናቸው።

ይሁን እንጂ፣ የሚከተሉት አሉታዊ ጎኖች ታይተዋል፡-

  • የአስተዳደር ውሳኔ አቤቱታ እና ምላሽ በቃል የሚስተናገድበት ሁኔታ መኖሩ።
  • ባለጉዳዩ የሰው ምስክር አቅርቦ የሚያሰማበት አሰራር አለመኖር።
  • ከአስተዳደር ውሳኔ ይዘት አንጻር በአዋጁ አንቀጽ 40 ላይ በተመለከተው መሰረት ጭብጥ አለመያዝ እና በቂ ማስረጃና የሕግ ትንተና አለማድረግ።
  • አልፎ አልፎ ውሳኔውን ለተገልጋዩ ከመስጠት ይልቅ ለሚያስፈጽሙ የመንግስት ተቋማት የመስጠት ልማድ መኖሩ።
  • የተቋቋመ የቅሬታ ማስተናገጃ አካል አለመኖር።
  • ግልጽና ወጥ የሆነ የቅሬታ አቀራረብ ሥነ-ሥርዓት ይፋ አለመደረጉ።

 

የቀረቡ ምክረ-ሀሳቦች

በዚህ የክትትል ሪፖርት መሰረት፣ የታዩ ክፍተቶችን ለማረም እንዲያስችል የሚከተሉት ምክረ-ሀሳቦች ቀርበዋል፡-

  • ለተቋሙ ሰራተኞች ስለአዋጁ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ማድረግ።
  • የአዋጁን የመመሪያ አወጣጥ ሂደቶችና የአስተዳደራዊ ውሳኔ አሰጣጥ መርሆዎችን የሚመለከታቸው ሁሉም የስራ ክፍሎች ተግባራዊ እንዲያደርጉ መዘርጋት።
  • አተገባበሩን በየጊዜው የሚከታተልና የሚያስተባብር አካል መፍጠር።
  • ተቋሙ በሚሰጣቸው ውሳኔዎች ላይ ለሚቀርቡ ማናቸውም ቅሬታዎች በአዋጁ መሰረት ወጥ የሆነ የቅሬታ ሰሚ ወይም ማስተናገጃ አካል ማቋቋም።
  • በአጠቃላይ የአስተዳደር ሥነ-ሥርዓት አዋጁ ላይ የተቀመጡ መርሆዎችንና ሂደቶችን ትኩረት በመስጠት ለመተግበር ቁርጠኛ መሆን።

ሪፖርቱን ያውርዱ

ተጨማሪ ሪፖርቶች