በንቃተ ሕግ ትምህርትና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት አዘጋጅነት የዐቃቤ ሕግ ሙያዊነትን በተመለከተ የፍትሕ ሚኒስቴር ዐቃቢያነ ሕግ እና የቡድን መሪዎች የተሳተፉበት የፓናል ውይይት ሰኔ 6 ቀን 2015 ዓ.ም በዳዓማት ሆቴል ተካሂዷል፡፡
ውይይቱን በንግግር የከፈቱት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የንቃተ ሕግ ትምህርትና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ እንዳልካቸው ወርቁ አንድ ተቋም ውጤታማ እንዲሆን ከተፈለገ የበቁ ሙያተኞች እንደሚያፈልጉት በመግለፅ ተቋሙን የሙያ ተቋም አድርጎ በመገንባት ሂደት ውስጥ ጉልህ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት ጠቁመዋል፡፡
በፓናል ውይይቱ የዐቃቤ ሕግነት ተሞክሯቸውን ያቀረቡት ዶ/ር ራስሙስ ፍትሕ ሚኒስቴር ለሙያዊነት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራበት መሆኑ የሚበረታታ እንደሆነ ገልጸው የዐቃቤ ሕግ ሙያተኝነት ተቋማዊ ግንባታ ሆኖ የራሱ የሆነ የሙያ ባህል ያለው ነፃ እና ገለልተኛ የሆነ ሙያተኛ መፍጠር ነው በማለት በተለያዩ ሀገራት ያላቸውን የዐቃቤ ሕግነት ተሞክሮ አጋርተዋል፡፡
በተቋሙ የቀድሞ አመራርና ዐቃቤ ሕግ በነበሩት አቶ እሸቱ ወ/ሰማያት እና በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ዘርፍ የቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች መከታተያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር በሆኑት አቶ ጌቱ ታደሰ ለውይይት መነሻ የሆኑ ተሞክሮዎች የተካተቱባቸው ሰነዶች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
ቀደም ሲልም የተቋሙ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮችን ያሳተፈ የፓናል ውይይት መጋቢት 07 ቀን ተካሂዶ የነበረ ሲሆን ይህ ለሁለተኛ ጊዜ የተደረገ ውይይት መሆኑ ተገልጿል፡፡