የዳኞችንና የፍትሕ አካላትን ክህሎት በማሳደግ የፍትሕ ስርዓቱን ለማሻሻል የሚያስችል የኤሌክትሮኒክ ትምህርት (E-learning) ስርዓት ከፍትሕ ሚኒስቴር ፤ከፌደራል ሕግና ፍትሕ ኢንስትቲውት፤ ከፌደራል ፍርድ ቤቶች የተወጣጡ ከፍተኛ አመራሮች፤ የስራ ሀላፊዎች ፤ ባለሙያዎች እና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ግንቦት 21/09/2017 ዓ.ም ተመርቋል፡፡
የፌደራል ሕግና ፍትሕ ኢንስትቲውት ዳይሬክተር ክቡር አምባሳደር ደግፌ ቡላ በመድረኩ ባስተላለፉት መልዕክት፣ አሁን የተዘረጋዉ የኤሌክትሮኒክ ትምህርት ስርዓት በቀጣይ የሚኖረንን ተቋማዊ አሠራር ለማሳደግ እና ለማዘመን ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
የፍትሕ ሚኒስቴር የተቋም ግንባታና ሪፎርም ዘርፍ ሚኒስትር ዲኤታ ክቡር ኤርምያስ የማነብርሃን (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ እንደ ሀገር የፍትሕ ስርዓቱን ለማዘመንና ለማጠናከር እንዲሁም በዲጂታ ኢትዮጵያ የተያዘዉን ግብ እዉን ለማድረግ የኤሌክትሮኒክ ትምህርት ስርአቱ ጠቀሜታዉ የጎላ በመሆኑ በቀጣይም በክልል ለሚገኙ ዳኞች፤ዐቃቢያነ ህጎች፤ ሬጂስትራሮች እና የምርመራ ባለሙያዎች ሳይቀር ተደራሽ እንደሚሆን ተናግራዋል፡፡
አክለዉም ስርአቱ በጋራ ለመሥራት እና የሚገጥሙንንም ችግሮች በጋራ ለመፍታት ከማገዙም በላይ ቦታ ሳይገድበን የገፅ ለገፅ ሥልጠናዎችን የሚተካ ከመሆኑ አኳያ በየትኛውም ቦታ ሆነን መማር እንደምንችል ትልቅ ማሳያ መሆኑን ገልጸው ፤ ስርዓቱ እንደ ተቋም የሥልጠና አሰጣጣችንን የላቀ እና ወጪ ቆጣቢ ለማድረግ የሚያስችለን ነው ብለዋል፡፡
በምረቃ ስነስርአቱ ወቅት ለታዳሚዎች ስለኤሌክትሮኒክ ትምህርት ስርአቱ አጠቃቀም እና ሂደቱን አስመልክቶ ሰፋ ያለ ማብራሪያ በባለሙያዎች አማካኝነት ቀርቧል፣ ከተሳታፊዎች ለተነሱ ጥያቄዎችም ምላሽ ተሰጥቷል፡፡
በመጨረሻም በመድረኩ የኤሌክትሮኒክ ትምህርት ስርአቱን እውን ለማድረግ ተሳትፎ ላደረጉ የስራ ሀላፊዎች እና ባለሙያዎች እንዲሁም የአዉሮፓ ህብረት እና ጂ.አይ.ዜድ ላበረከቱት ድጋፍ ዕውቅና ተሰጥቷል፡፡