የአዲስ አበባ ከተማ ሀገራዊ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ገጽታዋንና ደረጃዋን ለማስጠበቅ በሚያስችል ዘርፈ ብዙ የልማትና መልካም አስተዳደር የለውጥ እንቅስቃሴ የፌደራል መንግሥት ካስቀመጠዉ የተለያዩ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ጥብቅ ትስስርና መስተጋብር ያለው ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና ፍትሀዊነትን ያማከለ የአሠራር ሥርዓት መዘርጋት ተገቢ በመሆኑ፤
በዚህ ረገድ በከተማው እያደገ ከመጣው የልማት እንቅስቃሴ ሁለንተናዊ የልማት ትርጉም እንዲኖረውና አስተማማኝ የመልካም አስተዳደር ስርዓት ግንባታ አካል የሆነውን ለሕዝብ ጥቅም ሲባል የነበሩበትን የመሬት ይዞታ የሚለቁ ባለይዞታዎችን ግልጽ፣ ተጠያቂነትና ፍትሀዊ በሆነ አግባብ ለማስተናገድ የሚያስችል በወጡት የሕግ ማእቀፎች መሠረት የአፈጻጸም መመሪያ ማዘጋጀት አስፈላጊ በመሆኑ፤
የመሬት ልማትና ማኔጅመንት ፖሊሲን መሠረት በማድረግ የአደረጃጃት ለውጥ በመደረጉ፤ እንዲሁም የተሻሻለው የሊዝ አዋጅ፣ ደንብና መመሪያ በመጽደቃቸው ለሕዝብ ጥቅም ሲባል በሚለቀቁ ቦታዎች ላይ ለሰፈረ ንብረት ስለሚከፈል ካሳ እና ለለቀቁት መሬት ስለሚሰጥ የካሳ ግምት፣ የምትክ ቦታ እና ምትክ ቤት አሰጣጥ መመሪያ ቁጥር 3/2002 እንደገና ማሻሻል አስፈላጊ በመሆኑ፤
ለሕዝብ ጥቅም ሲባል የመሬት ይዞታ የሚለቀቅበትንና በይዞታው ላይ ለሠፈረው ንብረት ካሳ የሚከፈልበትን ሁኔታ ለመወሰን በወጣው አዋጅ ቁጥር 455/1997 አንቀጽ 14 ንዑስ አንቀጽ 2 በተሰጠው ሥልጣን መሠረት የአዲሰ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ ይህን የተሻሻለ የአፈጻጸም መመሪያ አውጥቷል፡፡