የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ንግድ ሚኒስቴር፣ ከመሠረታዊ የንግድ ዕቃዎች መሀከል ለህብረተሰቡ ለምግብ ፍጆታ ከሚውሉት ሸቀጦች ስኳር፣ ፖልም የምግብ ዘይት፣ ስንዴና የስንዴ ዱቄት ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ የታየባቸዉን እና ይኸው ክስተት በህብረተሰቡ የእለት ተዕለት ኑሮ ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ያስከተሉትን በጥናት በመለየት ግብይታቸውና ስርጭታቸው ላይ ክትትልና ቁጥጥር ማድረግ ጠቀሜታ እንዳለው የታመነበት በመሆኑ ፤
የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግሥት በኑሮ ውድነት የተነሳ በህብረተሰቡ ላይ የደረሰውን ተጽእኖ ለመቀነስና ገበያውን ለማረጋጋት ሲል በከፍተኛ ዋጋ ገዝቶ በድጎማ በዝቅተኛ እና በመካከለኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ላሉ የህብረተሰብ ክፍሎች ለማሰራጨት የሚያቀርባቸውንና ቀደም ሲል ያሰራጫቸውን የምግብ ፍጆታ ሸቀጦች ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ ለማስቻል በፌደራል መንግስቱ፣ በክልል መነግስታት፣ ተጠሪነታቸው ለፌደራሉ መንግሥት በሆኑ የከተማ አስተዳደሮች እና በመላ ሀገሪቱ በተዋረድ በሚገኙ የመንግሥት አስተዳደር እና ሌሎች አካላት ጨምሮ ሸቀጦቹን በመግዛት፣ በመሸጥ ፣ በማጓጓዝ፣ በማከማቸት ለህብረተሰቡ በማሰራጨትና መሰል ተግባራት ሂደት ውስጥ ስለሚኖራቸዉ ድርሻና ኃላፊነት ወጥነት ያለው የአፈፃፀም፣ የክትትል፣ የድጋፍ አሰጣጥና የቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ፤
የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ንግድ ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊከ የአስፈፃሚ አካላት አደረጃጀት ለመወሰን በወጣው አዋጅ ቁጥር 916/2008 ዓ.ም አንቀጽ 22 ንዑስ አንቀጽ 8 መሠረት ያህን መመሪያ አውጥቷል፡፡