የኢትዮጵያ የሒሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድ በአዋጅ ቁጥር 857/2014 መሠረት በርካታ ሥልጣን እና ተግባራት የተሰጡት ሲሆን ከእነዚህ ሥልጣን እና ተግባራት መካከል አንዱ ሪፖርት አቅራቢ አካላትን የሕዝብ ጥቅም ያለባቸው አካላት ወይም አነስተኛና መካከለኛ ድርጅቶች ብሎ መለየት የሚያስችል መስፈርት ማውጣት እና መመዝገብ ነው።
በዚሁ መሠረት ቦርዱ የሪፖርት አቅራቢ አካላትን የሥራ ዓይነት ወይም ባህሪ፣ የሀብት መጠን ወይም የሠራተኛ ቁጥር ከግምት ውስጥ በማስገባት የሕዝብ ጥቅም ያለባቸው ሪፖርት አቅራቢ አካላት እና አነስተኛና መካከለኛ ድርጅቶች የሚለዩበትን መስፈርት አስቀምጧል።
በተጨማሪም እነዚህ ሪፖርት አቅራቢ አካላት በአዋጁ በተደነገገው የፋይናንስ ሪፖርት ደረጃዎች መሠረት ኦዲት የተደረገ የሂሳብ መግለጫቸውን አዘጋጅተው ለቦርዱ መቼ ማቅረብ እና ማስመዝገብ እንዳለባቸው እንዲሁም በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ባያቀርቡ ያለባቸውን ኃላፊነት በዚህ መመሪያ ውስጥ እንዲካተት ተደርጓል።