በአዲስ አበባ ከተማ ያለውን የመሬት ይዞታና አስተዳደር በተሻለና ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲሁም ውስን የሆነውን የመሬት ሀብት አጠቃቀም በተገቢው ሁኔታ ለማስተዳደር፤ ህገወጥነትን ለመከላከል እንዲያስችል የከተማው አስተዳደር ልዩ ትኩረት ሰጥቶበት በ2002ዓ.ም መመሪያ ቁጥር 2/2002ዓ.ም ማውጣቱ ይታወሳል፡፡ በዚህም መሠረት መመሪያው ከወጣበት ቀን ጀምሮ የመሬት ይዞታ አገልግሎቶችን በመመሪያዉ መሠረት ሲሰጥ ከመቆየቱም በላይ የተሟላ የይዞታ ባለመብትነት ሰነድ የሌላቸዉን ባለይዞታዎችን የሬጉላራይዜሽን መስተንግዶ እየሰጠ ይገኛል፡፡
ይህ በእንዲህ እያለ አዲስ የሊዝ አዋጅ በመውጣቱና የመዋቅር ለውጥ በመደረጉ እንዲሁም በነባሩ መመርያ ላይ በትግበራ ወቅት አንዳንድ ክፍተቶች በመታየታቸው እና በመመሪያው ያልተዳሰሱ ጉዳዮች በመገኘታቸው መመርያውን እንደ አዲስ ማስተካካልና ማውጣት አስፈላጊ ሆኗል፡፡
የከተማ ቦታ በሕግ ለሚፈቀድላቸዉ ሰዎች እና ሰነድ ያላቸው ህጋዊ ባለይዞታዎች የሚጠይቋቸውን የተለያዩ መስተንግዶዎች ከሊዝ አዋጁና አዋጁን ለማስፈጸም ከወጣው ደንብ ጋር በተጣጣመ መልኩ ምላሽ ለመስጠት እንዲቻል መመሪያውን ለማሻሻል በማሰብ የከተማው አስተዳደር በተሰጠው ሥልጣንና ኃላፊነት መሠረት ይህ መመሪያ ለከተማው አስተዳደር ካቢኔ ቀርቦ ይህ የይዞታ አስተዳደር መመሪያ ቁጥር31/2013 ዓ.ም ወጥቷል፡፡