የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጽዳት አስተዳደር ኤጄንሲ የከተማ አስተዳደሩ ተቋማትን መልሶ ለማቋቋም በወጣው አዋጅ ቁጥር 74/2014 እንደተሻሻለ አንቀጽ 53 መሠረት ደረቅ ቆሻሻን ለማስተዳደርሥልጣን የተሰጠው ተቋም ነው ፡፡ በተሰጠው ሥልጣን መሰረተ የተቀናጀ ደረቅ ቆሻሻ አስተዳደርን ለማስፈን እና የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት እና ራዕዩን አውን ለማድረግ የሚያስችሉ የህብረተሰቡን ግንዛቤ የማሳደግ፣ ፈጣን የደረቅ ቆሻሻ አገልግሎት የበመስጠት፣ ደረቅ ቆሻሻን ጥቅም ላይ የማዋልና መወገድ የሚገባውን ደረቅ ቆሻሻ ጤናማ በሆነ መልኩ የማስወገድ አሰራሮችን በመተግበር ላይ ይገኛል ፡፡ ከሚሰጣቸው በርካታ የደረቅ ቆሻሻ አገልግሎቶች መካከል በቀጥታ ከህብረተሰቡ ጋር ግንኙነት ያላቸውና የቅሬታ ምንጭ የሆኑት ደረቅ ቆሻሻን የመሰብሰብና የማጓጓዝ አገልግሎቶች ናቸው ፡፡ ከ650 ሽ በላይ ለሚሆኑ አባዋራዎች እማዋራዎች እና ከ9 ሽ በላይ ለሚሆኑ ተቋማት ደረቅ ቆሻሻ ሰብስቦ ለማጓጓዝ በመንግሥት አቅም ብቻ ሊሰራ የማይችል በመሆኑ ኤጄንሲው በሚከፍለው የአገልግሎት ክፍያ ተመን መሠረት አገልግሎቶቹ በሶስተኛ ወገን እንዲሰጡ ተደርጓል ፡፡ ከመኖሪያ ቤቶች የሚመነጨውን ደረቅ ቆሻሻ በጥቃቅንና አነስተኛ የተደደራጁ ዜጎች ቤት ለቤት እየሄዱ የመሰብሰብ አገልግሎቱን እንዲሰጡ ሲደረግ ከመኖሪያ ቤት ውጪ ላሉ ተቋማትና ድርጅቶች ደግሞ የግል ባለሀብቶች በዘርፉ እንዲሰማሩ በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ መሠረት በርካታ የግል የጽዳት ድርጅቶች በህጋዊ መንገድ ተመዝግበው ደረቅ ቆሻሻን ከተለያዩ ተቋማት በመሰብሰብና በማጓጓዝ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡
ነገር ግን ለጥቃቅንና አነስተኛ ጽዳት ሽርክና ማህበራት የአሠራር መመሪያ የተዘጋጀ ቢሆንም የግል የጽዳት ድርጅቶች ለማስተዳደር የአገልግሎት አሰጣጥ መመሪያ ባለመኖሩ በግል ጽዳት ድርጅቶች የሚሰጠው አገልግሎት እንዴት እንደሚሰጥና በአገልግሎት አሰጣጡ የሚፈጠሩ የአሠራር ግድፈቶች እንደት ይታረማሉ የሚለውንና የመሳሰሉትን ጉዳዮች ለመተግበር አስቸጋሪ ሆኗል ፡፡ ስለዚህ ይህንን ችግር በዘላቂነት ለመፍታትና ተጠያቂነትን የሚያረጋግጥ አገልግሎት ለመስጠት እንዲያስችል የየግል የጽዳት ድርጅቶች የአገልግሎት አሰጣጥ የአሠራር መመሪያ ማዘጋጀት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡
በመሆኑም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጽዳት አስተዳደር ኤጄንሲ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርአሰፈፃሚ አካላትን መልሶ ለማቋቋም በወጣው አዋጅ ቁጥር 74/2014 እንደተሻሻለ አንቀጽ 15 ንዑስ አንቀጽ 2 (ሠ) በከተማው ካቢኔ በተሰጠው መመሪያ የማውጣት ሥልጣን መሠረት ይህን የግል የጽዳት ድርጅቶች የአሠራር መመሪያ አውጥቷል፡፡