ባለሥልጣን መ/ቤቱ በአዋጅ ከተሰጠው ከፍተኛ ሀገራዊ ኃላፊነት አኳያ ዓለምአቀፍ ሕግጋት፣ ደንብና ተቀባይት ያላቸውን መመሪያዎች ጠብቆ (SRPs) የመሥራት ግዴታ አለበት፡፡ በአዋጅ ከተሰጠው ኃላፊነት አንዱ ከአደጋና ከስጋት ነፃ የሆነ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት መስጠት ሲሆን ይህንን አገልግሎት የሚሰጡ ባለሙያዎች ከሥራው ባህሪ አንፃር በየጊዜው የጤንነት ምርመራ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡
ባለሥልጣን መ/ቤቱ የዓለምአቀፍ ሲቪል አቪዬሽን ድርጀት ባወጣው መስፈርትም ሆነ ከሙያው ጋር ተያያዥ በሆነ መመሪያ መሠረት በየአራት ዓመቱ የጤንነት ሁኔታ ማስመርመርና በኦዲት ወቅትም የባሙያዎቹን የጤንነት ሁኔታ ማረጋገጫ ማስረጃ የማቅረብ ዓለምአቀፍ ግዴታ ነው፡፡ በኦፕሬሽንና ቴክኒካል ሥራ ሂደት ላይ የሚቀጠሩ አዳዲስ ሠራተኞችንም አሰልጥኖ ለመቅጠር በቅድሚያ የጤንነት ምርመራ የሚደረገው ራሱን የቻለ የአቪዬሽን ሜዲካል አሴሰር ባለበት የጤና ተቋም ብቻ ነው፡፡ ባለሥልጣን መ/ቤቱ ከዓለምአቀፍ ግዴታ ከመወጣት ባሻገር የአቪዬሽን ዘርፍ እድገት ለማስቀጠል የሠራተኞችን ደኅንነትና ጤንነት የመጠበቅና ምቹ የሥራ አካባቢን የመፍጠር ኃላፊነት አለበት፡፡
ባለሥልጣን መ/ቤቱ ይህንን ለመፈፀም የሚያስችል የአሠራር ሥርዓት በመዘርጋት ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ በመሆኑም አገልግሎት አሰጣጡን በመመሪያ በማስደገፍ ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ በባሥልጣን መ/ቤቱ ባለው መካከለኛ ክሊኒክና ከሌሎች የጤና ተቋማት ጋር የአገልግሎት ስምምነት ውል በመግባት እየተሰጠ ይገኛል፡፡ ሆኖም ካለው ነባራዊ ሁኔታ በመመሪያው የተካተቱት አንቀፆች ይዘት በርካታ ክፍተቶችና ችግሮች ያሉበት በመሆኑ ለአፈፃፀም ሆነ ለክትትል አስቸጋሪ አድርጎታል፡፡
ስለሆነም የህክምናው አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት ያለው እንዲሆን፣ ለህክምና የተመደበው በጀት ኢኮኖሚያዊ/የገንዘብ ምጣኔን ባገናዘበ መልኩ ለመጠቀምና በአፈፃፀም ሂደት ያሉትን ክፍተቶችን በመለየት እርምጃ ለመውሰድ እንዲቻል መመሪያውን ፈትሾ ማስተካከል ተገቢ ከመሆኑም በላይ በኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን መቋቋሚያ አዋጅ 616/2001 አንቀጽ 92/2 መሠረት ባለሥልጣን መ/ቤቱ መመሪያ የማውጣት ሥልጣን ስለተሰጠው ሥራ ላይ የነበረውን መመሪያ ለመተካት የወጣ አዲስ መመሪያ ነው፡፡