የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 141/2000 የተቋቋመና በመንግሥት የልማት ድርጅቶች ማቋቋሚያ አዋጅ ቁጥር 25/1984 መሠረት የሚተዳደር ኮርፖሬሽን ነው ፡፡ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን በማቋቋሚያ ደንቡ እንደተገለፀው የባቡር ትራንስፖርት መሠረተ ልማትንና የባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት ለማካሄድ የተቋቋመው አዲስ የልማት ድርጅት ሲሆን፣ በቅርቡ በሥራ ላይ ከዋለው ድርጅታዊ መዋቅር ጋር የተጣጣመ የሥራ መሪዎች የሚተዳደሩበት ደንብ ማውጣት አስፈላጊ በመሆኑና የሥራ መሪዎች ተግባርና ኃላፊነት በኮርፖሬሽኑና በኮርፖሬሽኑ ሠራተኛ ማህበር መካከል በተደረገ የህብረት ስምምነት እንዲሁም በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ ስለማይሸፈን ኮርፖሬሽኑ የሥራ መሪዎች የሚመሩበትና የሚተዳደሩበት ደንብ ማውጣት አስፈለጊ ሆኖ በመገኘቱ፡፡ በኮርፖሬሽኑማቋቋሚያ ደንብ ውስጥ የተጠቀሰውን ዓላማ ለማሳካት፣ ብቁና ታታሪ የሆኑ መሪዎች መመደብና በአንፃሩም ይዞ ለመቆየት እንዲቻል መብትና ግዴታ የሚያስከብር የመተዳደሪያ ደንብ በሥራ ላይ ማዋል ተቀዳሚ ተግባር በመሆኑ፣ ይህ የሥራ መሪዎች መተዳደሪያ ደንብ ተዘጋጅቷል፡፡