ኢ-ሰርቪስ ዜጎችና የንግድ ማኅበረሰብ አካላት ኤሌክትሮኒካዊ የአገልግሎት መጠየቂያ ቅጾችን በመሙላትና አስፈላጊ ሰነዶችን ስካን አድርጎ በማያያዝ ከየትኛውም ቦታና ጊዜ የአገልግሎት ጥያቄያቸውን ማቅረብ የሚችሉበት የኢንተርኔት አገልግሎት ነው፡፡ ከዚህም በላይ የአገልግሎት ሂደት መከታተያ ልዩ ቁጥርን በመጠቀም የጠየቁት አገልግሎት የደረሰበትን ሂደት መከታተል፣ በአካል መቅረብ በሚያስፈልግበት ወቅት የቀጠሮ ቀን መያዝ፣ ወቅታዊ መልዕክቶችን በኢ-ሜይል እና በአጭር የፅሑፍ መልዕክት መቀበል፣ እንዲሁም ለቀጣዩ አገልግሎት አሰጣጥ ጠቃሚ የሆኑ አስተያየቶችን ለመስጠት ይችላሉ።
እነዚህን የኤሌክትሮኒካዊ አገልግሎቶች ጠቀሜታ በመረዳት፣ የመገናኛና የመረጃ ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከግብርና ሚኒስቴር፣ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ከከተማ ልማት፣ቤቶችና ኮንስራክሽን ሚኒስቴር፣ ከመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ፣ ከኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና ጤና እንክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን፣ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ ከንግድ ሚኒስቴር፣ ከመንግሥት ሰራተኞች ማኅበራዊ ጥበቃ ባለሥልጣን የተወጣጣ ከ60 በላይ ትራንዛክሽናል አገልግሎቶችን ተግባራዊ አድርጓል፡፡
ኤሌክትሮኒካል አገልግሎቶች ከሚሰጡ መንግስታዊ ተቋማት መካከልም የከተማ ልማት ቤቶችና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር አንዱ ሲሆን አራት አገልግሎቶች ተመርጠው ኤሌክትሮኒካዊ በሆነ መልኩ ተገልጋዮች እንዲጠቀሙባቸው አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል፡፡ በሚኒስቴር መሥሪያ ቤታችን ኤሌክትሮኒካዊ በሆነ መልኩ ለጊዜው ለተገልጋይ ጥቅም መስጠት የጀመሩት አራቱ ሰርቪሶች
1. የኮንስትራክሽን አገልግሎት ሰጪዎች ምዝገባ አገልግሎት፣
2. የኮንስትራክሽን ባለሙያዎች ምዝገባ አገልግሎት፣
3. የፕራክቲሲንግ ባለሙያዎች ምዝገባ አገልግሉት፣
4. የኮንስትራክሽን መሳሪያዎች ምዝገባ አገልግሎት ናቸው፡፡
ከላይ የተጠቀሱትና ሌሎች ወደፊት የሚካተቱ ኤሌክትሮኒካል አገልግሎቶችን ለአገልግሎት ተጠቃሚዎች (ደንበኞች) የተቀላጠፈና ዘመናዊ የሆነ አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችል እንዲሁም አላስፈላጊ ምልልስን በማስቀረት ጊዜያቸው፣ ጉልበታቸውና ሃብታቸው ከብክነት ተጠብቆ ደንበኛች አጥጋቢና ውጤታማ አገልግሎት ማግኘት እንዲችሉና አገልግሎት የሚሰጡትና የሚያስተዳድሩ ሠራተኞችም ተጠያቂነትና ኃላፊነት እንዲኖራቸው ለማድረግ የኢ-ሰርቪስ አስተዳደርና አጠቃቀም መመሪያ ማዘጋጀት አስፈልጓል፡፡