መንግሥት ለትምህርት ሴክተሩ በተለይም ለከፍተኛ ትምህርት ፍትሃዊ ተደራሽነት በሰጠው ልዩ ትኩረት ከጊዜ ወደ ጊዜ በዘርፉ ከፍተኛ ለውጥ እየተመዘገበ መጥቷል፡፡ ይሁን እንጂ የመንግሥት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሰፋ ያለ መዋዕለ ነዋይ የሚፈስባቸው ግዙፍ የግንባታ ስራዎች የሚከናወንባቸው እና ለመማር ማስተማር፣ ለምርምርና ማኅበረሰብ አገልግሎት በርካታ ወጪ የሚፈልጉ በባህሪያቸው ከሌሎች ሴክተሮች የተለዩ በመሆናቸውና ሴክተሩ በመንግሥት የሚመደበውን ሀብትም ይሁን ተቋማት በራሳቸው የሚያመነጩት ሀብት ለተቋማት ተልዕኮ መሳካት እንዲያውሉት አስቻይ የሆነ ግልጽ ሥርዓት እንዲኖራቸው በማስፈለጉ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በመንግሥት በጀት ለሚሸፈኑ ወጪዎች የክፍያ ተመን መመሪያ ቁጥር 56/2011 ወጥቶ በሥራ ላይ መዋሉ ይታወቃል፡፡
ሆኖም በመመሪያው አፈፃፀም ባጋጠሙ ችግሮችና በተለይም በ2003 ዓ/ም ከወጣው የመምህራን የትርፍ ሰዓት ክፍያ መመሪያ ጋር በተያያዘ ያጋጠመውን የአተገባበር ችግር በማስመልከት በተደጋጋሚ የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች እየተነሱ ስለሚገኙ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ጥያቄዎች በሚመልስ መልኩ ማስተካከል አስፈልጓል፣
እንዲሁም ተመን ያልወጣላቸው ክፍያዎችና ተመኖች በመኖራቸውና የተሻሻለ የአሠራር ሥርዓት ለመዘርጋት ያስችል ዘንድ ተመኖችና ተመን ያልወጣላቸው ክፍያዎች ትክክለኛ የአሠራር ሥርዓት ለመፍጠር እና የነበረውን የአሠራር ክፍተት ለመዝጋት ይህንን መመሪያ ማውጣት አስፈልጓል፡፡
በመሆኑም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በመማር ማስተማር፣ በጥናትና ምርምር፣ በማኅበረሰብ አገልግሎት፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በተቋም አመራርና አስተዳደር፤ እንዲሁም የመማር ማስተማሩን ሂደት በተግባር ትምህርት ለሚያግዙ የቴክኒክ ረዳትነት ስራዎች ከጫና በላይ እና ከመደበኛ ስራ ውጪ ለተከናወኑ ተግባራት የሚከፈሉ ክፍያዎችን ተመን በወጥነት በማዕከል በማዘጋጀት የሚከፈሉ ክፍያዎች ሕጋዊ መሠረት እንዲኖራቸው በማድረግ የሕዝብና የመንግሥት ሃብት አጠቃቀም ውጤታማነት ለማስጠበቅ ይህ መመሪያ ወጥቷል፡፡