በኢንቨስትመንት ደንብ ቁጥር 474/2012 መሠረት ውስን የንግድ ዘርፎችን ከውጭ ኢንቨስትመንት ውድድር በመከለል የአገር ውስጥ ባለሀብቶችን በብዛት እና በጥራት ለማፍራት፤ ከአለም-አቀፉ የንግድ ትሥሥር ሥርዓት ጋር ይበልጥ እንዲተዋወቁ ለማስቻል፤ በሂደትም እሴትን ወደሚጨምሩ የኢንቨስትመንት መስኮች እንዲሸጋገሩ በማድረግ በአገር ውስጥ አቅሞች ላይ የተመሠረተ ዘላቂ ሀገራዊ ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚያስችል ፖሊሲ ተግባራዊ ሲደረግ የቆየ መሆኑን በመገንዘብ፤
በፖሊሲው አፈፃፀም ውስን ውጤቶች ቢመዘገቡም ይህ አሠራር ተግባራዊ ማድረግ ከተጀመረበት የጊዜ ማዕቀፍ አንፃር የሚጠበቀውን ዓላማ በሚፈለገው መጠን ማሳካት ካለመቻሉም በላይ፡ ከለላ የተሰጣቸው የንግድ ዘርፎች ሰፊ የአገልግሎት ተደራሽነት፡ የጥራት እና የብቃት ችግሮች የሚታይባቸው በመሆኑ፡ ለህገ-ወጥ ድርጊት የተጋለጡበት ሁኔታም እየተስፋፋ በመምጣቱ፤
እንዲሁም የተከለሉት የንግድ ሥራ ዘርፎች ለፍትሀዊ ውድድር ያልተጋለጡ ከመሆናቸው እና ከቁጥጥር ስርአቱ አተገባበር ውስንነት ጋር በተያያዙ ምክንያቶች የፖሊሲውን ዓላማ የተገዳደሩ ተጨማሪ ክፍተቶች በመስተዋላቸው፤
ለአገር ውስጥ ባለሃብት የተከለሉ የወጪ፡ የገቢ፡ የጅምላ እና የችርቻሮ ንግድ ኢንቨስትመንት ዘርፎችን የሚመለከተው ሀገራዊ የፖሊሲ እሳቤ በአዲስ ተሻሽሎ ዘርፎቹ ፍላጎትና አቅሙ ላላቸው የውጭ ባለሀብቶች ደረጃ በደረጃ እንዲከፈቱ በማድረግ የፖሊሲ አፈፃፀሙን በተግባር እየፈተሹ እና በሂደትም ለውጥ እና ጥቅሞችን በመመዘን እያሰፉ የመሄድ አቅጣጫን መከተል አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ፡
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ቦርድ በኢንቨስትመንት አዋጁ አንቀጽ 6(4) እና አንቀጽ 31(1)(ሠ) በተሰጠው ሥልጣን መሠረት ይህን መመሪያ አውጥቷል፡፡