የእንስሳት ጤንነትን ለመጠበቅና ምርታማነታቸውን ለማሳደግ የሚያስፈልጉ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገሮች ተመርተው ወደ አገር ዉስጥ የሚገቡና ከአገር የሚወጡ የእንስሳት መድኃኒቶችና መኖ እንዲሁም ሌሎች ግብዓቶች አመራረት፣ አቅርቦትና አጠቃቀም በሚፈለገው ጥራትና ደረጃ ተሟልተው ለተጠቃሚ እንዲደርሱና አገራችንን ከንዑስ ዘርፉ በበለጠ ተጠቃሚ ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ ይሄንን ዘርፍ በበላይነት እንዲመራ በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፑብሊክ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የእንስሳት መድኃኒትና መኖ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን በአዋጅ ቁጥር 728/2004 እንዲቋቋም ተደርጓል፡፡
ስለሆነም በእንስሳት መድኃኒት እና መኖ ንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ ድርጅቶች ከዉጪ ወደ ሀገር የሚያስገቡት ወይም ከሀገር ወደ ዉጪ የሚልኩት የእንስሳት መድኃኒት እና መኖ ጥራትና ደኅንነት ማረጋገጥ አስፈላጊ በመሆኑ፤
በእንስሳት መድኃኒት እና መኖ ላይ በቂና ሕጋዊ ቁጥጥር ለማካሄድ የሚያስችል ሥርዓት መዘርጋት አስፈላጊ በመሆኑ፤
በመግቢያና መዉጫ ኬላዎች ላይ የሚደረግ የእንስሳት መድኃኒት እና መኖ ንግድ ቁጥጥር ሥራዎች ግልጽና ተጠያቂነት በሰፈነበት አሠራር እንዲካሄዱና ተገልጋዮችም ይህንን አውቀው የሚጠበቅባቸውን ቅድመ ዝግጅቶች በማሟላት የአገልግሎት ጥያቄያቸውን በአግባቡ እንዲያቀርቡ ለማስቻል፤
የኢትዮጵያ የእንስሳት መድኃኒትና መኖ አስተዳዳርና ቁጥጥር ባለሥልጣን በአዋጅ ቁጥር 728/2004 አንቀጽ 28 ንዑስ አንቀጽ 2 በተሰጠው ሥልጣን መሠረት ይህን የእንስሳት መድኃኒትና መኖ የመግቢያ እና መውጫ ፈቃድ አሰጣጥ እና ቁጥጥር መመሪያ አውጥቷል፡፡