የሕግና ፍትሕ አገልግሎት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ክቡር አቶ በላይሁን ይርጋ በኦሮሚያ ክልል ቄለም ወለጋ ዞን ደምቢ ዶሎ ከተማ የሚገኙ አንዳንድ የኦሮሞ ባህላዊ ፍርድ ቤቶችን አሠራር ምልከታ አደረጉ።
ቄለም ወለጋ ዞን፣ ደምቢ ዶሎ ከተማ፡- ክቡር ሚኒስትር ዴኤታው ከቄለም ወለጋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ገመቹ ጉርሜሳ፣ ከደምቢ ዶሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ታደሰ እና ሌሎች የደምቢ ዶሎ ከተማ፤ የደምቢ ዶሎ ዩኒቨርሲቲ አመራሮች ጋር በመሆን በከተማው የሚገኙ አንዳንድ የኦሮሞ ባህላዊ ፍርድ ቤቶችን አሠራር የጎበኙ ሲሆን፣ በምልከታውም ባህላዊ ፍርድ ቤቶቹ በመደበኛው ፍርድ ቤት ረጅም ጊዜ ይወስዱ የነበሩ ጉዳዮች በአጭር ጊዜ ወጪ ቆጣቢ በሆነ መንገድ እና የከሳሽና ተከሳሽን ጥቅምና ፍላጎት ከግምት ውስጥ ባስገባ መልኩ እልባት እየሰጡ ስለመሆኑ መረዳት ተችሏል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ የፍትሕ ትራንስፎርሜሽን ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እየተደረገ ሲሆን፣ በዚህ ፍኖተ ካርታ ውስጥ አንዱ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ የመሰረተ-ማኅበረሰብ ፍትሕ ነው። መሰረተ ማኅበረሰብ ፍትሕን ተግባራዊ ከማድረግ አንፃር የገዳ ፍርድ ቤቶች ወይም የኦሮሞ ባህላዊ ፍርድ ቤቶች በክልሉ ውስጥ ከፍተኛውን ሚና እየተወጡ ሲሆን፣ ክልሉ እነዚህን ፍርድ ቤቶች እውቅና የሚሰጥ ሕግ አውጥቶ ስራ ላይ በማዋሉ ባህላዊ ፍርድ ቤቶቹ እስከታችኛው የቀበሌ መዋቅር ድረስ ተደራጅተው ለበርካታ ጉዳዮች እልባት እየሰጡ ይገኛሉ።
እንዲህ አይነት ባህላዊ ፍርድ ቤቶች በሌሎች ክልሎችም በሰፊው እንዲስፋፉ ፍትሕ ሚኒስቴር ለክልሎች ድጋፍ እያደረገ ሲሆን፣ ሲዳማ ክልል እና አማራ ክልልም እነዚህን ፍርድ ቤቶች እውቅና የሚሰጥ ሕግ አውጥተው በመተግበር ላይ ይገኛሉ።