በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ፍትሕ ሚኒስቴር የንቃተ ሕግ፤ ትምህርት እና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት አስተባባሪነት የፌደራል እና አዲስ አበባ የሙስና ወንጀል መርማሪ ፖሊሶችን ክህሎት ማሳደግ የሚያስችል የአቅም ግንባታ ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡
የንቃተ ሕግ ትምህርትና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ እንዳልካቸዉ ወርቁ እንደገለፁት ሥልጠናዉን መስጠት ያስፈለገዉ በልዩ ሁኔታ የሙስና ወንጀል ምርመራ ላይ የመርማሪዎችን ክህሎት ለማሳደግ እንደሆነና፣ ዓላማውም መርማሪ ፖሊሶች በምርመራ ወቅት ምን ላይ ማተኮር እንደሚገባቸዉ በቂ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ነው ብለዋል፡፡
ፍትሕ ሚኒስቴር የሙስና ወንጀሎችን ለመከላከል ከመርማሪ ፖሊሶች ጋር በቅንጅት እንደሚሰራ የገለፁት ዳይሬክተሩ፣ ከዚህ ቀደም ተመሳሳይ ሥልጠናዎች ከፌደራል፤ አዲስ አበባ እና ክልሎች ለተዉጣጡ መርማሪ ፖሊሶች መሰጠቱን አውስተዋል፡፡
በፍትሕ ሚኒስቴር የሙስና ወንጀል ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ጄኔራል ፣ዳይሬክተር ጄነራል አቶ ዘላለም ፈቃዱ በበኩላቸዉ በአሁኑ ወቅት ሙስና የሀገርን ኢኮኖሚ እያዛባ መሆኑን ገልጸዉ፣ የወንጀል አፈጻጸሙም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየረቀቀ እና ወንጀለኞችም ስልታቸዉን እየቀያየሩ መምጣታቸዉን ተከትሎ ወንጀሉን በተገቢዉ ሁኔታ ለመከላከል የሕግ አካላትን እዉቀትና ክህሎት ማሳደግ አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል ብለዋል፡፡
ሥልጠናዉ በዋናነት ስለ ሙስና ጽንሰሀሳብ፤ የሙስና ወንጀሎች ጥቆማ እና ወንጀሉ ከተፈጸመ በኋላ በሚደረጉ ልዩ የምርመራ ዘዴዎች ላይ ያተኮረ ሲሆን፤ የሙስና ወንጀል ምርመራ ሌሎች መደበኛ ወንጀሎችን ለመመርመር በምንከተለዉ የምርመራ ሂደት ልንደርስበት ስለማንችል ልዩ ዘዴዎችን መከተል እንደሚያስፈልግ በሥልጠናው ወቅት የተመላከተ ሲሆን፣ ሰለወጣኞች ሥልጠናዉ ሲጠናቀቅ የሙስና ወንጀል ምርመራ በሚመራበት ሂደት ላይ በቂ ግንዛቤ እንደሚኖራቸው ተጠቁሟል፡፡
በመጨረሻም ከሰልጣኞች ለተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች በአሰልጣኞች አማካኝነት ሰፋ ያለ ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡