መግቢያ
መንግሥት የዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ አድገትን ለማፋጠን ክፍተኛ ኃላፊነት አለበት፡፡ ይሄን ኃላፊነት ለመወጣት መንግሥት የራሱ ገቢ ያስፈልገዋል፡፡ የሄንኑ ስራ የሚያከናውንበትን ገቢ ከሚያሰባስበብበት የገቢ ምንጭ መካከል ግብር አንዱና ዋነናው መሆኑ ይታወቃል፡፡ ለዚህም ነው ግብር ወይም ታክስ ዋናው የመንግሥት የፋይናንስ ምንጭ በመሆን የአንድ አገር ኢኮኖሚ ልማትንና እና እድገት የጀርባ አጥንት ነው ሲሉ በዘርፉ ባለሞዎች የሚገልጹት፡፡
በዚህም ምክኒያት ማንኛውም መንግሥት በአለማችን ታሪክ ሀገራት ከተመሰረቱበት ጊዜ ጀምሮ በዜጎች እና በመንግሥት መካከል በተፈጸመ ማኅበራዊ ውል መሠረት ዜጎች መንግሥት የሚባለውን አካል ፈጥረው ህይወታቸውን፣ ነጻነታቸውን፣ እና ንብረታቸውን ሊደርስባቸው ከሚችል ማንኛውም ጣልቃ ገብነት እንዲከላከልላቸው በመፈለግ መንግሥትን ቃል በማስገባት እነሱም እንደዜጋ መንግሥት ለዚሁ አገልግሎት መስጫ ወጪ መሸፈኛ የሚሆነውን የገቢ ምንጭ ስለሚያስፈልገው ግብር መክፈልን እንደግዴታ ወስደው በመስማማት በየግዜው ይሄንኑ ግዴታቸውን በውላቸው መሠረት በመክፈል መንግሥትም በበኩሉ ተቀዳሚ እና ጥንታዊ ግዴታው የሆነውን የዜጎችን ሰላምና ጸጥታ ለማስጠበቅ በውሉ መሠረት እንዲከውን ይሆናል፡፡
በዘመናዊው የአለማችን እውነታ ደግሞ መንግሥት ጥንታዊ ከሆነው የዜጎችን ሰላም እና ደኅንነት ማስከበር አልፎ የህብረተሰብን መሠረታዊ ፍላጎት ለማሟላት መሰረተ ልማትን ማስፋፋት እና የዜጎችን ሁለንተናዊ እድገትን ለማፋጠን የሚያስፈልጉ ስራዎችን እንዲያከናውን እና ማኅበራዊ ፍትሕን እንዲያሰፍን ይጠበቃል፡፡ ይሄንን ተግባር ለመከወን መንግሥት ወጪውን የሚሸፍንበት የራሱ የገቢ ምንጭ ያስፈልገዋል፡፡ ግብር ደግሞ ዋነኛው የገቢ ምንጭ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ሌላው ገቢ ከመንግሰት አገልግሎት የሚሰበሰብ ክፍያ፣ ከተለያዩ አካለት የሚገኝ እርዳታ፣ እና የመሳሰሉትን እንደ የመንገስት የገቢ ምንጭ መጥቀስ ይቻላል፡፡
ጠቅለል አድርገን ስናየው ግብር ወይም ታክስ ማለት መንግሥት ለጠቅላላው ህብረተሰብ ጥቅም ሲባል የሚያወጣቸውን ወጪዎች ለመሸፈን እንዲችል ማንኛውም ግብር ከፋይ በተለየ ሁኔታ ለከፈለው ግብር በግሉ ቀጥተኛ የጥቅም ጥያቄ ሳያነሳ የሚከፍለው በሕግ የተጣለ የግዴታ ክፍያ ነው፡፡ ከዚህ ትርጉም ለመረዳት እንደሚቻለው:-
- ግብር በሕግ የሚጣል ግዴታ ነው- በፍላጎት ሳይሆን በግዳጅ የሚከፈል ነው፡፡ይሄም ቀድሞ በተደነገገ ሕግ መሠረት የሚፈጸም ነው፡፡ አለመክፈልም በወንጀል ሕግ እና በአስተዳደር ሕግ ያስጠይቃል፡፡
- ግብር የሚጣለው እና የሚሰበሰበው በመንግሥት ብቻ ነው፡፡ ግለሰቦች ግብር የመጣል እና ሰብሰብ ሥልጣን የላቸውም፡፡
- ታክስ የሚከፈለው በታክስ ከፋይ ነው፡፡ የተፈጥሮ ወይም በሕግ ሰውነት የተሰጠው ሰው ሊሆን የችላል።
- ታክስ የሚጣለው እና የሚሰበሰበው ለጠቅላላው ህብረተሰብ ጥቅም ነው። በመንግሥት ወጪ ከሚሰጥ አገልግሎት ሁሉም ተጠቃሚ ነው ግብር ከፋዩ ብቻ አይደለም፡፡
- ታክስ ከፋዩ ለከፈለው ግብር ቀጥታ ከመንግሥት በግሉ ልዩ ጠቅም የመጠየቅ መብት የለውም፡፡ ግብር የሚከፍለው መንግሥት ለሚያከናውናቸው የልማት ተግባሮች እገዛ የማድረግ ግዴታ ስላለበት ነው፡፡
ግብር ሁለት መሠረታዊ ጉዳዮች ያሉት ሲሆን እነሱም ግብር የሚጣልበት የገቢ ምንጭ(tax base) እና የሚጣለው ግብር ወይም ታክስ መጠን(tax rate) ናቸው፡፡ ግብር የሚጣልባቸው የገቢ ምንጮች ገቢ የሚያስገኙ ማናቸውም የምርት፣ የአገልግሎት እና የንግድ ወይም የስራ ዘርፍ ሲሆኑ የግብር መጠን ደግሞ በእነዚሁ ገቢዎች ላይ የሚጣለው የግብር መጠን ነው፡፡ በዚህም ግብር ከፋዩ በገቢው ልክ ግበር የሚከፍል ሲሆን ትንሽ ገቢ ያለው ግብር ከፋይ ትንሸ ግብር የሚከፍል ሲሆን ትልቅ ገቢ ያለው ግብር ከፋይ እንዲሁ ከፍ ያለ ግብር ይከፍላል ማለት ነው፡፡ ይህም የግብርን አፈጻጸም ፍትሀዊነት ያሳያል፡፡
የግብር ዓላማ
ግብር የተለያዩ ዓላማዎችን ለማስፈጸም የሚሰበሰብ ሲሆን ጥቂቶቹን ለማየት ያክል፡-
- ገቢን ለመፍጠር
- ከላይ እንዳነሳነው ግብር ዋነኛው የመንግሰት የገቢ ምንጭ ነው፡፡
- የገቢ እና የሀብት ልዩነትን መቀነስ
- በሀብታምና በደሀ መካከል ያለውን ልዩነት ለመቀነስ ዕየጨመረ የሚሄድ የታክስ ሥርዓት ተግባራዊ ያደረጋሉ፡፡ በዙሁም መሠረት ከፍተኛ ገቢ የሚያገኙ ከፍተኟ ታክስ መካከለኛ ገቢ ያላቸው መካከለኛ ታክስ ሲከፍሉ ዝቅተኛ ገቢ የሚያገኙ ደግሞ ከታክስ ነጻ ይደረጋሉ፡፡ ከከፍተኛና መካከለለኛ ታክስ ከፋዮች የሚሰበሰበው ገቢ ለዝቅተኛ እና ገቢ ለሌላቸው መደጎሚያ ይሆናል፡፡
- ኢኮኖሚን ለማረጋጋት
- መንግሥት ታክስን በመጠቀም የዋጋ ግሽበትን እና የእኮኖሚን መቀዛቀዝን ለመቆጣጠር ሊጠቀምበት ይችላል፡፡የሄውም የሚፈጸመው የታክስ መጠንን በጨመር ወይም በመቀነስ ወይም አዲስ ታክስ በመጣል ወይም በማንሳት ሊሆን ይችላል፡፡
- ጎጂ ወይም መሠረታዊ ያልሆኑ ምርቶችን ፍጆታ መቀነስ
- በህብረተሱ ጤና ላይ ችግር ይፈጠራሉ ተብለው ለሚታሰቡ ምርቶች ወይም መሠረታዊ ባልሆኑ ምርቶች ፍጆታ ለመቀነስ መንግሥት ታክስን በመጠቀም ከገበያ እንዲገለሉ ማድረግ /እንዲቀንሱ ማድረግ የችላል፡፡ከፍተኛ ታክስ በመጣል አብዛኛው ህብረተሰብ እነኘህኑ ምርቶች ከመግዛት እንዲቆጠብ ማድረግ ይቻላል፡፡
- ኢንቨስትመንትን ማበረታታት
- መንግሥት ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት ሴክተሮችን በመለየት ለተወሰነ ጊዜ የታክስ እፎይታ ሊፈቅድ ወይም ታክስ ሊቀንስላቸው የችላል፡፡
- ለሀገር ውስጥ ምርት እና አምራቾች ጥበቃ ማድረግ
- ከውጭ የሚገቡ ምርቶች ላይ ከፍ ያለ ታክስ በመጣል ለሀገር ውስጠ ምርት እና አምራቾች ጥበቃ ሊያድርግ ይችላል
- የውጭ ንግድን ማበረታታት
- የውጭ ንግድን ለማበረታታት እና የውጭ ምንዛሬን ለመጨመር መንግሥት ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን ከታክስ ነጻ ሊያደርጋቸው ይችላል፡፡
በአገራችን የግብር ወይም የታክስ ሥርዓት ስናይ በኢ.ፌ.ድ.ሪ ህገመንግሰት እና በታክስ ሕግጋት መሠረት መንግሥት የተለያዩ የግብር ወይም ታክስ አይነቶችን የሚጥል እና የሚሰበስብ ሲሆን እነዚህን የግብር አይነቶች ስናይ፣- የገቢ ግብር፣ የተርን ኦቨር ታክስ፣ የተጨማሪ እሴት ታክስ፣ እና ኤክሳይስ ታክስ ይገኙበታል፡፡ እያንዳንዱ የግብር አይነት የራሱ የሆነ ባህርያት ያሉት ሲሆን በድምር ግቡ የመንግሥትን ገቢ ከፍ በማድረግ መንግሰት መሰረተ ልማት በማስፋፋት እና አጠቃላይ የአገሪቷን ኢኮኖሚ ከፍ እንዲያደርግ ማስቻል ነው፡፡
ግብር መክፈል ግዴታ መሆኑን ከግብር ባህሪት አንጻር ያነሳን ሲሆን በአጋራችን የግብር ሕግጋትም ይሄው ተደንግጎ ይገኛል፡፡ የገቢ ግብር በተመለከተ የገቢ ግብር አዋጅ ቁጥር 979/2008 አንቀጽ 7 እና 9 መሠረት ማንኛውም ኢትዮጵያ ነዋሪ ያልሆነ ሰው ከኢትዮፕያ ውስጥ ላገኘው ገቢ የገቢ ግብር የመክፈል ግዴታ አለበት እንዲሁም ማነኛውም የኢትዮጵያ ነዋሪ ከየትናውም የአለም አገር ላገኘው ገቢ የገቢ ግብር የመክፈል ግዴታ እንዳለበት በግልጽ ደንግጓል፡፡ ከተጨማሪ እሴት ታክስ አንጻር ስናየው በአዋጅ ቁጥር 1341/2016 አንቀጽ 6 እና ቀጥሎ ባሉ አንቀጾች መሠረት ከእያንዳንዱ ግብር የሚከፈልበት ግብይት የተጨማሪ እሴት ታክስ መክፈል ግዴታ መሆኑን ደንግጓል፡፡ በሌላ በኩል ኤክሳይስ ታክስን ስናይ ህጉ ለህበረተሰብ ጤና ጎጂ የሆኑ እንዲሁም ከመሠረታዊ ፍልጎት ባለፈ የቅንጦት ምርቶች ላይ የሚጣል የግብር አይነት ሆኖ በኤክሳይስ ታክስ አዋጅ ቁጥር 1186/2012 አንቀጽ 6 መሠረት እነኝኑ ምርቶች የሚያመርቱም ሆነ ከውጭ የሚያስገቡ አስመጪዎች እንዲሁም ኤክሳይስ ታክስ የተጣለባቸውን አገልግሎቶች የሚሰጡ ሰዎች በህጉ በዝርዝር በተጣለባቸው መጠን የኤክሳይስ ታክስ የመክፈል ግዴታ አለባቸው፡፡ እንደማሳያ ሶስቱን ያነሳን ሲሆን ሌሎች ከላይ ያነሳናቸው የግብር አይነቶችም እንዲሁ በተመሳሳይ ሁኔታ ግዴታን ይጥላሉ፡፡
በዚሁ አግባብ ግብር መክፈል ግዴታ ከሆነ ግብርን በተገቢው ጊዜ አለመክፈል በህጉ ተጠያቂነትን የሚያስከትል ሲሆን ጥቂት ነጥቦችን ለማንሳት፡፡
- በፌደራል ታክስ አስተዳደር አዋጅ ቑጥር 983/2008 አንቀጽ 116 እና ቀጥሎ ባሉት ድንጋጌዎች መሠረት ከግብርን አለመክፈል፣ማጭበርበር፣ ግብር መሰወር፣ ቫት ማጭበርበር እና በጠቅላላለው ከታክስ ጋር ተያይዘው ለሚፈጸሙ ወንጀሎች በእስር እና እንደየ ወንጀሉ ክብደት በብርም የሚያስቀጡ ናቸው፡፡
- በኤክሳይስ ታክስ አዋጅ ቁጥር 1186/2012 አንቀጽ 39 እና ቀጥሎ ባሉት ድንጋጌዎች መሠረት ኤክሳይስ ታክስን አለመክፈል ከሶስት ዓመት ጽኑ እስራት ጀምሮ በተለያየ ደረጃ በእስር እና በገንዘብ እንደሚያስቀጣ ተደንድንግጓል፡፡
- በሁሉም የግብር ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች ከወንጀል ተጠያቂነት በተጨማሪ አስተዳደራዊ ቅጣቶችን ያስከትላሉ እሱም በገንዘብ፣ ከስራው ማገድ እና የመሳሰሉትን አስተዳደራዊ እርምጃዎች ያስከትላል፡፡
ስለዚህ ግብር መክፈል ለሀገር እድገት እና ለዜጎች ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ.ማኅበራዊ፣እና ፖለቲካዊ መብቶች መረጋገጥ ካለው ፋይዳ አንጻር አስፈላጊ ከመሆኑም ባለፈ በአንድ ሉኣላዊ አገር ግብርን ለመንግሥት መክፈል ግዴታ ሲሆን ይሄን አውቆ በወቀቱ አለመክፈል የወንጀል እና አስተዳደራዊ ቅጣቶችን ያስከትላል፡፡ ስለዚህ ሁሉም ግብር ከፋይ የሚጠበቅበትን ግብር ሁሉ በጥንቃቄ በወቅቱ መክፈል አለበት፡፡
በንቃተ ሕግ፣ ትምህርትና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ