መግቢያ
በማህረሰቡ ዘንድ ስር ሰዶ የቆየ ለአካል ጉዳተኝነት ያለው የተሳሳተ ግንዛቤ በአካል ጉዳተኞች የሥራ ስምሪት መብት ላይ የራሱን አሉታዊ ተጽኖ ያደረሰ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡ ስለሆነም ኢትዮጵያ አካል ጉዳተኛ የሆኑ ዜጎቿ የሚደርሰባቸው ከሥራ ቅጥር ማግለል ወይም መድሎ ለማስወገድ የአካል ጉዳተኞች የሥራ ስምሪት መብት አዋጅ በ2000 ዓ.ም እንዲወጣ አድርጋለች፡፡ በዚህ ጽሁፍም የአካል ጉዳትተኛን ምንነትና በአዋጁ የተመለከቱ መብቶችን እንመለከታለን፡፡
አካል ጉዳተኛ የሚባለው ማን ነው?
አካል ጉዳተኛ የሚለው ቃል በተለያየ መንገድ የተለያየ ትርጉም ያለው ሲሆን ለዚህ ጽሁፍ ዓላማ ሲባል ከሥራ ስምሪት ጋር በተገናኘ የተሰጠውን ትርጉም እንመለከታለን፡፡ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ አካል ጉዳተኛ የሚለው ቃል ሲተረጎም “በደረሰበት የአካል ወይም የአምሮ ሰላም፣ የስሜት ህዋሳት ጉዳት ምክንያት ፕሮፌሽናል ሥራዎችን ወይም መደበኛ ሥራን ለማስራት የተገደበ ወይም በአካል ጉዳቱ ምክንያት ማኅበራዊ ወይም ባህላዊ ተግባራትን ለማከናወን የተገደበ ሰው እንደሆነ ትርጉም የተሰጠው ሲሆን አዋጅ ቁጥር 568/2000 አንቀጽ 2(1) ላይ አካል ጉዳተኛ ማለት የደረሰበትን የአካል፣ የአዕምሮ ወይም የስሜት ህዋሳት ጉዳት ተከትሎ በሚመጣ የኢኮኖሚያዊ፣ የማኅበራዊ ወይም የባህላዊ መድሎ ሳቢያ በሥራ ስምሪት የእኩል እድል ተጠቃሚ ያልሆነ ሰው ነው” በማለት ትርጉም ሰጥቶታል፡፡
የአካል ጉዳተኞች የሥራ ቅጥር ሁኔታ
በማስታወቂያ በወጣ ክፍት የሥራ ቅጥር ላይ የተወዳደር አካል ጉዳተኛ የወጣው የሥራ ቅጥር የሥራው ጠባይ ወይም ባህሪ የማይፈቅድ ካልሆነ በቀር አስፈላጊ የችሎታ መመዘኛዎችን ካሟላ እና በውድድሩ ከፍተኛ ነጥብ ካመጣ የመቀጠር መብቱ የተጠበቀ ሲሆን በውድድሩ ያመጣው ነጥብ ከሌሎች ተወዳዳሪዎች ጋር የተቀራረበ ወይም እኩል ነጥብ የሆነ እንደሆነ ቅድሚያ የመቀጠር መብት አለው፡፡ በሌላ በኩል በማንኛውም መስሪያ ቤት ወይም ድርጅት ውስጥ ያለን ክፍት የሥራ ቦታ በዕድገት፣ በድልድል ወይም በዝውውር የመያዝ ወይም በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ አገር በሚሰጥ የሥልጠና ፕሮግራም ለመሳተፍ መብት ያለው ሲሆን ከላይ በተዘረዘሩት የቅጥር ሁኔታና ሥልጠና አካል ጉዳተኛ የሆነ ሠራተኛ ያመጣው ነጥብ ከሌሎች ጋር የተቀራረበ ወይም እኩል ከሆነ ቅድሚያ የማግኘት መብት አለው፡፡
የተከለከለ ተግባርና መድሎ የተከለከለ ስለመሆኑ
ማንኛውም የሥራ ቅጥር ማስታወቂያ ሲወጣ በማስታወቂያው ላይ የሚዘረዘሩት የመወዳደሪያ መስፈርቶች ለሥራው ባህሪ አስገዳጅ ካልሆነ በስተቀር በተወዳዳሪው ላይ ያለውን ጉዳት የሚመለከት መስፈርት ማውጣት የተከለከል መሆኑ በአዋጁ አንቀጽ 4(3) ተደንግጓል፡፡ የሥራው ጠባይ ወይም ባህሪ ማለት የሚሰራው ሥራ ለአካል ጉዳተኛ የማይሆን የሥራ አይነት ሲሆን ለምሳሌ የውትድርና ማለትም እንደ ፖሊስና መከላከያ ባለ ተቋም ለመቀጠር ምንም አይነት የአካል ጉዳት መኖር እንደሌለበት የሚታወቅ ነው፡፡ በመሆኑም በነዚህ ተቋማት ለመቀጠር አንዱና ዋናው መስፈርት ምንም አይነት የአካል ጉዳት የሌለበት መሆን እንዳለበት ያስገድዳል፡፡ ከዚህ ውጪ የአካል ጉዳተኛን እኩል የሥራ እድል የሚያጣብብ ሕግ፣ አሠራር፣ ልምድ፣ ዝንባሌ መፍጠር ህገ ወጥ ሲሆን በቅጥር፣ በእድገት፣ በድልድል፣ በዝውውር ወይም በሌሎች የሥራ ስምሪት ሁኔታዎች ለማወዳደሪያ የሚቀመጡ መስፈርቶች የአካል ጉዳተኞችን የሥራ እድል የሚያጠብ ሆኖ ከተገኘ እንደመድሎ የሚቆጠር ነው፡፡
የአሰሪ እና የአካል ጉዳተኛ ሰራተኞች ኃላፊነት
ለማንኛውም ሠራተኛ የሥራ ቦታ ምቹና ሳቢ መሆን ያለበት ሲሆን በተለየ ሁኔታ ግን አካል ጉዳተኞች በሚሰሩበት ቦታ የመስሪያቤቱ ወይም አሰሪው
- የሥራና የሥልጠና አካባቢን የማመቻቸትና ተስማሚ የሆኑ የሥራ ወይም የሥልጠና መሳሪያወችን የማሟላት፣
- ማንኛውም ረዳት የሚያስፈልገው አካል ጉዳተኛ ሥራውን ለመሥራት ወይም ሥልጠናውን ለመከታተል እንዲችል ረዳት የመመደብ፣
- ሴት አካል ጉዳተኞች በጾታ እና በአካል ጉዳት ምክንያት ያለባቸውን ተደራራቢ ጫና ያገናዘበ ማስተካከያና የድጋፍ እርምጃዎችን የመውሰድ እንዲሁም በሥራ ቦታ የሚደርስባቸውን ጾታዊ ጥቃት የመከላከልና ተፈፅሞ ሲገኝም በፈፃሚው ላይ ህጋዊ ርምጅ የመውሰድ ወይም እንዲወሰድ የማድረግ ኃላፊነቶች አሉበት፡፡
በሌላ በኩል አካል ጉዳተኛ ሠራተኛ በተመደበበት ሥራ በሙሉ ኃላፊነት የማከናወን ግዴታ ያለበት ሲሆን የሥራውን ኃላፊነት በትክክል ባይወጣ ወይም ጥፋት ቢፈፅም አካል ጉዳቱ ከተጠያቂነት የማያድነው መሆኑን አዋጁ አንቀጽ 8 በግልፅ ደንግጎ ይገኛል፡፡
የአካል ጉዳተኛ ሥራ ስምሪት መብት ሲጣስ ምን አይነት እርምጃ የወሰዳል?
በአዋጅ ቁጥር 568/2000 የተቀመጡትን ድንጋጌዎችና አዋጁን ለማስፈፀም የወጡ ደንብና መመሪያወችን የተላለፍ አሰሪ የወንጀል ተጠያቂነት እንዳለበትና የቅጣቱም መጠን ከብር 2,000 (ሁለት ሺ) የማያንስና ከብር 5,000 (አምስት ሺ) የማይበልጥ መቀጮ እንደሆነ ተቀምጧል፡፡ በወንጀል ህጉ የበለጠ የሚያስቀጣ በሆነ ጊዜ ግን በወንጀል ህጉ የተመለከተው ቅጣት ተፈፃሚ ይሆናል፡፡
ሌላው በዚህ አዋጅ የተሸፈነው የመብት ጥሰት ሲያጋጥም ክስ በማን ይመሰርታል? ለሚለው ጥያቄ ምላሽ ሲሆን በዚህም መሠረት በአዋጁ ላይ የተቀመጡ ድንጋጌዎች ወይም አዋጁን ለማስፈፀም የወጡ ደንቦችና መመሪያዎች ባለመከበራቸው መብቱ የተጣሰበት የአካል ጉዳተኛ ወይም አካል ጉዳተኛው አባል የሆነበት የአካል ጉዳተኖች ማህበር ወይም አካል ጉዳተኛው አባል የሆነበት የሰራተኞች ማህበር ወይም አዋጁን የሚያስፈፅም አግባብ ያለው አካል ሥልጣን ላለው ፍርድ ቤት ክስ የማቅረብ መብት ያለው መሆኑ በአዋጁ አንቀጽ 10 ተደንግጓል፡፡ ይህን የሕግ ክፍል ስንመለከት በህገ መንግስቱ አንቀጽ 37 ላይ የተቀመጠውን ፍትሕ የማግኘት መብት አስፍቶ መብት የሰጠ ሲሆን የአካል ጉዳተኛው የሥራ ስምሪት መብት ሲጣስ መብቱ የተጣሰበት ግለሰብ ብቻ ሳይሆን ሌሎች አባል የሆነባቸው ማህበራትም ክስ ማቅረብ አንደሚችሉ የሚያሳይ ነው፡፡
በዚህ አዋጅ ሌላው የተሸፈነው ጉዳይ ክስ ሲመሠረት የማስረዳት ሸክምን በተመለከተ ሲሆን በነባራዊው ሁኔታ አንድ ሰው ክስ ሲመሰርት ለክሱ መነሻ የሆነውን ምክንያት በተገቢ ሁኔታ ማስረዳት እንዳለበት የተቀመጠ ሲሆን በአካል ጉዳተኛ የስሥራ ስምሪት መብት ግን በአካል ጉዳቱ ምክንያት ብቻ በቅጥር፣ በእድገት፣ በድልድል፣ በዝውውር ወይም በሌሎች የሥራ ሁኔታዎች ላይ መድሎ ተፈፅሟል በሚል ጭብት በማስያዝ ብቻ ክስ መመስረት የሚቻል ሲሆን ክስ የቀረበበት ወገን ድርጊቱ አድሏዊ እንዳልነበረ በማስረጃ ማረጋገጥ አለበት በማለት የማስረዳት ሸክሙን ወደ ተከሳሽ አዙሮታል፡፡
ማጠቃለያ
አካል ጉዳተኞች በአካል ጉዳታቸው ምክንያት በሥራ ስምሪት ሂደት አድሎ እንዳይፈፀምባቸው የሕግ ጥበቃ የተደረገላቸው እንደመሆኑ አሰሪዎች እነዚህን መብቶች ሳይሸራረፉ መተግበር የሚጠበቅባቸው ሲሆን ሌሎች የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላትም ለህጉ መፈፀም የበኩላቸውን ኃላፊነት ሊወጡ ይገባል፡፡
በንቃተ ሕግ ትምህርትና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ