በኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 47 የተደነገገውን ዜጎች በመሬት ላይ ለሚገነቡት ቋሚ ንብረት የተጎናጸፉት የባለቤትነት እና በመሬት የመጠቀም መብታቸውን በከተሞች ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ፤
የከተማ መሬት ይዞታ መመዝገብ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ አስተማማኝ መረጃን በማመንጨት ለሚፈለገው አገልግሎት ለማዋል ተቋማዊ መሠረት በመሆኑ፤ በተለይም የዜጎች ይዞታ መብት ዋስትና እንዲያገኝና የከተሞችን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና አካባቢያዊ ልማት ማፋጠን አስፈላጊ በመሆኑ፤
ከመሬት እና ከማይንቀሳቀስ ንብረት ጋር ተያይዞ የሚነሳውን ክርክር ለመቀነስ፣ ባለይዞታው በሕግ አግባብ ያፈራውን ሀብት መጠቀም የሚያስችለው ግልፅነትና ተጠያቂነት ያለበት አስተማማኝ የሆነ የአሰራር ሥርዓት መዘርጋት እና በመንግስት የሚሰጡ አገልግሎቶች የተሳለጡ እንዲሆኑ ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ፤
ከመሬት ይዞታ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን መብቶች፣ ክልከላዎች እና ኃላፊነቶችን ለመመዝገብ የሚያስችል ወቅታዊ፣ ፈጣን፣ ከገበያ ልውውጥ ጋር የተጣጣመ የሕግ ማዕቀፍ በማውጣት የመሬትና የማይንቀሳቀስ ንብረት ለነፃ ገበያ የኢኮኖሚ ሥርዓት ግንባታ ያለውን አስተዋጾ ለማሳደግ፣ እንዲሁም ማንኛውም የመሬት ባለይዞታ በመሬት ላይ ላፈራው የማይንቀሳቀስ ንብረት በመሬት ይዞታው ውስጥ ዋስትና ማረጋገጫ እንዲኖረው ማድረግ በማስፈለጉ፤
የህጋዊ ካዳስተር መሠረታዊ መርሆዎች የሆኑትን የይዞታ ምዝገባን፣ በይዞታ ልውውጥ ጊዜ የባለይዞታን ይሁንታ ማግኘት፣ የይዞታ ምዝገባን ለሕዝብ ግልጽ ማድረግ እና ይዞታውንና ባለይዞታውን በመለያ ኮዶች መለየትን ሥራ ላይ ማዋል በማስፈለጉ፤
በኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ-መንግስት አንቀፅ 55 (2)(ሀ) መሠረት የሚከተለው ታውጇል፡፡
•
•