በፌዴራል የመንግሥት ተቋማት የፍትሐብሔር ጉዳዮች አያያዝ ክትትል ግኝት ሪፖርትን መነሻ በማድረግ ከፌደራል መንግሥት ባለ በጀት መስሪያ ቤቶች እና የልማት ድርጅቶች ከፍተኛ አመራሮች ጋር መስከረም 29 ቀን 2018 ዓ.ም ውይይት ተካሄደ፡፡
የውይይት መድረኩ በ2017 በጀት ዓመት በፌዴራል የመንግሥት ተቋማት ላይ በተደረጉ የፍትሐብሔር ጉዳዮች አያያዝ ክትትል የተገኙ ግኝቶች ላይ የጋራ መግባባት ላይ በመድረስ በቀጣይ ተጠናክረው ሊቀጥሉ የሚገባቸውን ጉዳየች አጠናክሮ ለማስቀጠል፣ ሊሻሻሉ የሚገባቸውን ጉዳዮች በማሻሻል እና የተሻለ የአሰራር ቅንጅትን በመፍጠር የመንግሥት እና የሕዝብን ፍትሐብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቅ እንዲቻል ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑ ተገልጿል፡፡
በውይይት መድረኩ የፌዴራል የመንግሥት ተቋማት የፍትሐብሔር ጉዳዮች አያያዝ ክትትል ግኝት ሪፖርት እና የፌዴራል የመንግሥት ተቋማት እርስ በእርስ ያልተግባቡባቸው የፍትሐብሔር ጉዳዮች የውሳኔ አሰጣጥ እና በውሳኔ አሰጣጥ ሂደት የተስተዋሉ ችግሮች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
በሪፖርቱ የተቋማት ክትትል ዓላማ፣ በክትትል የተገኙ ግኝቶች ፣በክትትል ወቅት ያጋጠሙ ችግሮች እና በቀጣይ ሊከናወኑ የሚገቡ ተግባራት በዝርዝር ቀርበዋል፡፡ የፌዴራል የመንግሥት ተቋማት በክትትል የሚሰጡ ምክረ ሃሳቦችን በመተግበር እንዲሁም ከፍ ያለ ዋጋ ባላቸውና በይዘታቸው ውስብስብ በሆኑ ውሎች ላይ ከድርድር ጀምሮ ውሉ እስከሚፈፀምበት ድረስ የፍትሕ ሚኒስቴር ተሳታፊ እንዲሆን በማድረግ የመንግሥት እና የሕዝብን ፍትሐብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቅ እደሚገባ በሪፖርቱ ተመላክቷል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ የፌዴራል የመንግሥት ተቋማት እርስ በእርስ ባልተግባቡባቸው የፍትሐብሔር ጉዳዮች የውሳኔ አሰጣጥ ሂደት ላይ በተቋማት በኩል የሚስተዋሉ ችግሮች ትኩረት ተሰጥቶ ሊስተካከሉ እንደሚገባ በውይይት መድረኩ ተገልጿል።
በውይይቱ የፍትሕ ሚኒስቴር ከሚያከናውናቸው ስራዎች መካከል የመንግሥት እና የሕዝብን ፍትሐብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቅ አንዱ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን፣ በዚህም የፌዴራል የመንግሥት ተቋማት አጠቃላይ የፍትሐብሔር ጉዳዮች አያያዝ ክትትል እና ድጋፍ እንዲሁም ተቋማት የሚቀርቡባቸውን የሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ ክሶች ድርድር በማድረግ በስምምነት እንዲያልቁ ጥረት በማድረግና ተቋማትን ወክሎ በመከራከር የሕዝብ እና የመንግስትን ጥቅም ከማስጠበቅ አንፃር ተጨባጭ ዉጤት መታየቱ ተገልጿል፡፡